ምንኵስናን “አደንዛዥ ዕፅ” የሚሉት የሆሳዕናው አባ ብንያም መንቾሮ ጵጵስና ይሻሉ፤ “ልጅ ሳልወልድ አልሞትም” እያሉ የሚዝቱ ቧልተኛና ሆድ አምላኩ ናቸው!
- የተሐድሶ ኑፋቄ አቀንቃኞችን፣ ለጉባኤ በመጋበዝና በማወደስ ግንባር ቀደም ናቸው
- ለቅዳሴ የተሠየሙትን ልብሰ ተክህኖ በማስወለቅ ለሥርዓቱ ንቀታቸውን አሳይተዋል
- በገና እና በሰኔ አጽዋማት ሉካንዳ ያዘወትራሉ፤ በሑዳዴም በጠዋት ገበታ ይሠየማሉ
- ውዳሴ ማርያም፣ ገድላት፣ ስግደት፣ ጾም፣ ፍትሐት፣ ንስሐ አያስፈልጉም፤ ብለዋል
- በጸሎተ ቅዳሴ ላይ ሳሉ በሞባይላቸው ፖርኖግራፊ ያያሉ፤ በፌስቡክ ቻት ያደርጋሉ
- ምንኵስናን “አደንዛዥ ዕፅ” በማለት እንደሕይወት ጥሪ ሳይኾን እንደሸክም ይቆጠራሉ
- “ለማግባት ባይሳካልኝም፣ ልጅ መውለዴ ግን የማይቀር ጉዳይ ነው፤” እያሉ ይዝታሉ
* * *
- ከሰዎች ጋር ዓምባጓሮ በፈጠሩ ቁጥር፣ ቆባቸውንና ልብሳቸውን በማሳየት፣ “ይህ አደንዛዥ ዕፅ (ምንኵስና) ይዞኝ እንጂ እያንዳንዳችኹን በጫማ ጥፊ ነበር የምዘረጋችኹ፤” በማለት በዐደባባይ የሚናገሩና ምንኵስናን እንደ ጸጋ ሳይኾን እንደ ሸክም የሚቆጥሩ ናቸው፤
- “ክርስቲያን መኾን ማለት በ40/80 ቀን ክርስትና መነሣት ወይም ነጭ ለብሶ ወደ ቤተ ክርስቲያን መምጣት አይደለም፤ ጌታን ተቀበል ሲሉህ አትከራከር፤ አትጨቃጨቅ፤ ወዳጄ፣ እጅህን አንሣና ጌታን ተቀበል፤” ሲል የተናገረውን በጋሻውን በመደገፍና በማሞካሸት፣ “እንዲኽ ዓይነት ደፋር መምህር በማጣታችን እስከ ዛሬ ተጎድተናል፡፡ ከዚኽ በኋላ ወደ ኋላ አንመለስም፡፡ የወንጌል ችቦ ይኸው እየበራላችኹ ነው፤” በማለት ለኑፋቄው ዘር ግልጽ ድጋፋቸውን አሳይተዋል፡፡
- “ሕዝብ ይወግረኛል ብዬ እንጂ ውዳሴ ማርያም፣ ገድላት፣ ስግደት፣ ጾም፣ ፍትሐት፣ ንስሐ… አስፈላጊ አይደሉም፤” በማለት ተናግረዋል፡፡ በቅዳሴ ሰዓት መቅደስ ውስጥ ተቀመጠው የሚዘገንኑና ጸያፍ ፊልሞችን በሞባይል ያያሉ፤ ስልክ ያናግራሉ፤ በፌስቡክ ቻት ማድረግም ቋሚ ሥራቸው ነው፡፡
- በገና እና በሰኔ አጽዋማት፣ ሆቴል ገብተው በሕዝብ መካከል ተመልካችን በሚያሳፍርና በሚያሸማቅቅ መልኩ የፍሥክ ምግቦችን በማዘዝ ይበላሉ፤ በይበልጥ ደግሞ በዐቢይ ጾም፣ ለተከታታይ ቀናት በጠዋት ሆቴል እየገቡና አልኮል እየጠጡ አጽዋማትን በመሻር የማሰናከያ አለት ኾነዋል፤
- ከተለያዩ ሴቶች ጋር ባልተለመዱና ለአገልግሎት በማይመቹ ሰዓታትና በድብቅ ቦታዎች በተደጋጋሚ ይታያሉ፡፡ ሚስት ማግባቱ ባይሳካላቸው እንኳ፣ ልጅ መውለዱ የማይቀር ጉዳይ እንደኾነ ተናግረዋል፤ “ልጅ ሳልወልድ አልሞትም” ሲሉ ይፎክራሉ፡፡
* * *
ቅዱስ ሲኖዶስ ተጨማሪ ኤጲስ ቆጶሳትን ለመሾም በያዘው ዕቅድ መሠረት፣ ከተጠቆሙት ቆሞሳት አንዱ፣ የሐዲያና ስልጤ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ አባ ብንያም መንቾሮ አንዱ ናቸው፡፡ ከ2001 እስከ 2005 ዓ.ም. በደብር አስተዳዳሪነት ከቆዩ በኋላ ሀገረ ስብከቱን በሥራ አስኪያጅነት በመምራት ላይ የሚገኙት ቆሞሱ፤ ለማዕርገ ጵጵስና እንደማይበቁ የሚገልጽ የተቃውሞ አቤቱታ ቀርቦባቸዋል፡፡
ትላንት፣ ሐምሌ 10 ቀን 2008 ዓ.ም. ከሆሳዕና ወደ አዲስ አበባ በመጓዝ፣ ለኤጲስ ቆጶሳት አስመራጭ ኮሚቴ የተቃውሞ አቤቱታቸውን ያቀረቡት ካህናትና ምእመናን፥ ሥራ አስኪያጁ ቆሞስ አባ ብንያም መንቾሮ፣ የተሰጣቸውን መንፈሳዊ አደራና የሥራ ሓላፊነት ያልተወጡ፤ ከመንፈሳዊ አባት የማይጠበቅ የሃይማኖት ሕፀፅና የሥነ ምግባር ጉድለት፤ የአስተዳደር በደልና የአቅም ማነስ የሚታይባቸው በመኾኑ ለታላቁና ለተቀደሰው ማዕርገ ጵጵስና መጠቆማቸውን ተቃውመዋል፡፡
አቤቱታቸው፣ በኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ ሥነ ሥርዓት ደንብ አግባብና በእግዚአብሔር ስም በእውነት የቀረበ መኾኑን ያረጋገጡት ካህናቱና ምእመናኑ፤ አስመራጭ ኮሚቴው፣ ከወገንተኛነት በጸዳ መልኩ ለነገዪቱ ቤተ ክርስቲያን በማሰብ፣ የበግ ለምድ የለበሱ ነጣቂ ተኵላዎችን በማስረጃዎች እየለየ በመወሰን ምርጫውን እንዲያካሒድ ተማፅነዋል፡፡
የሀገረ ስብከቱ ካህናትና ምእመናን በተወካዮቻቸው ተፈራርመው ያቀረቡት አቤቱታ፡–
• ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን
• ግብረ ምንኵስናን
• አስተዳደራዊ የማስፈጸም ብቃትን፤የሚመለከቱና በርካታ ንኡሳን ነጥቦች የተብራሩበት ነው፤ ሥራ አስኪያጁ ቆሞስ አባ ብንያም መንቾሮ፣ ለኤጲስ ቆጶስነት መመረጥና መሾም ቀርቶ፤ ቤተ ክርስቲያን የጣለችባቸውን አደራ በማናናቅ በሚያሳዩት ኢ-ክርስቲያናዊ ጠባይዕና በሞላባቸው የሃይማኖት ሕፀፅ ለምእመናን ማሰናከያ በመኾናቸው፣ ጉዳያቸው በቅዱስ ሲኖዶስ ደረጃ ተመርምሮ ከፍተኛ ውሳኔ እንዲተላልፍባቸው ጠይቀዋል፡፡
ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን አንፃር፤
የጠቅላይ ቤተ ክህነትንና የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮአዊና መዋቅራዊ አንድነት ለማናጋትና ለማፈራረስ ሌት ተቀን ከሚሠሩና ቅዱስ ሲኖዶሱ ካገዳቸው የተሐድሶ መናፍቃን ጋር አብረው፣ ኑፋቄውን ከሚያስተጋቡ ሰባክያንና ዘማርያን ነን ባዮች ጋር ጥልቅ ግንኙነት በመፍጠር፤ በአህጉረ ስብከቱ የተለያዩ ወረዳዎችና ከተሞች በተደጋጋሚ ለጉባኤ በመጋበዝ፤ ከቤተ ክርስቲያናችን አስተምሯችን ውጭ የኾኑ ስብከቶችና መዝሙሮች እንዲተላለፉ አድርገዋል፤ ምእመናን፣ ለእንግዳና ባዕድ ትምህርቶች እንዲጋለጡ፤ የሌሎችን እምነቶች እንዲለማመዱ በማድረግና ለተሐድሶ ኑፋቄ አቀንቃኞች መንገድ በመጥረግ ግንባር ቀደም ኾነዋል፡፡
በ2004 ዓ.ም. የበዓለ ትንሣኤ ሌሊት ዋዜማ፣ ኪዳን ተደርሶ ካበቃ በኋላ፣ ቆሞስ አባ ብንያም አርፍደው ወደ ቤተ መቅደስ ድንገት ዘው ይላሉ፡፡ ጸሎተ ኪዳን አድርሰው ለቅዳሴ የተሠየሙትና በዕድሜ የሚበልጧቸው፣ በምእመኑም ዘንድ ተወዳጅ የኾኑት ቆሞስ አባ ኃይለ ጊዮርጊስ ወደ ሥርዓተ ቅዳሴው በመግባት ላይ ነበሩ፡፡ ሕግ አፍራሹ አባ ቢኒያምም፣ “የደብሩ አስተዳዳሪ እኔ ነኝ፤ ልብሰ ተክህኖውን አውልቀህ ስጠኝ፤ እኔ ነኝ መቀደስ የሚገባኝ” ይሏቸዋል፡፡ አባ ኃይለ ጊዮርጊስም፣ “እኔ ልብሰ ተክህኖውን ከማወልቅ መጽሐፍ እይዛለኹ፤ እርስዎ ይቀድሱ” ቢሏቸውም ቆሞስ አባ ቢንያም ግን፣ በካህናት፣ በዲያቆናትና በምእመናን ፊት ሁከት በመፍጠር የተሠየሙትን ካህን በግድ አስወልቀው ሥርዓተ ቅዳሴው ተካሒዷል፡፡ በዕለቱም ለሥርዓተ ቤተ ክርስቲያናችን ያሳዩትን ትዕቢትና ንቀት የታዘቡ ካህናትና ዲያቆናት በእጅጉ አዝነውባቸዋል፡፡ ትሕትና የሌላቸው፣ ስሜታዊና ለሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን የማይገዙ ናቸው፡፡
በ2005 ዓ.ም. በሆሳዕና ደብረ ኃይል ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን፣ የወርኃ ሰኔ ቅዱስ ሚካኤል ክብረ በዓልን ምክንያት በማድረግ ከአዲስ አበባ ከጋበዟቸው አንዱ በጋሻው ደሳለኝ ነበር፡፡ አጉራ ዘለሉና ጥራዝ ነጠቁ በጋሻው በዕለቱ፡- “ክርስቲያን መኾን ማለት በ40/80 ቀን ክርስትና መነሣት አይደለም፤ ወይም ደግሞ፣ ነጭ ለብሶ ወደ ቤተ ክርስቲያን መምጣት አይደለም፤ ጌታን ተቀበል ሲሉህ አትከራከር፤ አትጨቃጨቅ፤ ወዳጄ፣ እጅህን አንሣና ጌታን ተቀበል፤” ሲል ተናግሯል፡፡ በዚኽ ኑፋቄው የተበሳጩ ምእመናንም ጉባኤውን አቋርጠው ወጥተዋል፡፡
በሰዓቱና በስፍራው ለቡራኬ የቆሙት አባ ቢንያም፣ የበጋሻውን ኑፋቄ በመደገፍና ግለሰቡን በማሞካሸት፣ “እንዲኽ ዓይነት ደፋር መምህር በማጣታችን እስከ ዛሬ ተጎድተናል፡፡ ከዚኽ በኋላ ወደ ኋላ አንመለስም፡፡ የወንጌል ችቦ ይኸው እየበራላችኹ ነው፤” በማለት ለኑፋቄው ዘር ግልጽ ድጋፋቸውን አሳይተዋል፡፡
በሆሳዕና ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤት አባሉና ሰባኪው ፈለቀ ሙሉጌታ፣ ባለበት የሃይማኖት ሕፀፅ የደብሩ ሰበካ ጉባኤ ከአገልግሎት ቢያግደውም ቆሞስ አባ ቢንያም ግን ፈቅደውለታል፡፡ ዘማሪው፣ “ማርያም ታምዳለች ብዬ ሰብኬና ዘምሬ አላውቅም” በማለት ከሰንበት ት/ቤቱ ሰብሳቢ ጋር ያደረገውን ሙግት፣ “አዎን ብዩአለኹ፤’’ ብሎ አምኗል፡፡ በተጨማሪም፣ በ2007 ዓ.ም. በዐቢይ ጾም የሆሳዕና ዕለት፣ “ጸሎተ ፍትሐቱ ተፈታም አልተፈታም ምን ዋጋ አለው፤ የሚፈታውም የሚያስረውም ኢየሱስ ነው፤” በማለት ተናግሯል፡፡ ሲናገር የሰሙት የሰንበት ት/ቤት ተማሪዎች ለሰበካ ጉባኤ በማቅረባቸው፣ ተጠርቶ ሲጠየቅ የተናገረውን በማመኑ በሰበካ ጉባኤው ከአገልግሎቱ በደብዳቤ ታግዷል፡፡ ቆሞስ አባ ቢንያም ግን፣ የታገደው የተሐድሶ መናፍቅ እንዲያገለግል በማድረግና እስከ አኹን ድረስ የተሐድሶ ኑፋቄውን እንዲኹም፣ የተሐድሶ መንፋቃንን ኅትመቶች ለሰንበት ት/ቤቱ ተማሪዎች እያከፋፈለ አመለካከቱን እያስፋፋ ይገኛል፡፡
በዚኹ ደብር ሚያዝያ 2008 ዓ.ም. ጉባኤ ለማካሔድ የደብሩ ሰበካ ጉባኤ ዝግጅት ሲያደርግ መምህራንን የጋበዙት ሥራ አስኪያጁ ቆሞስ አባ ቢንያም፣ ሰበካ ጉባኤው የማይፈልጋቸውን መምህራን በማምጣታቸው ጉባኤው ወደ ደብረ ገነት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ተዛውሯል፡፡ በዚኹ ጉባኤ የተጋበዘው በጋሻው ደሳለኝ፡- “በጻድቃን ስም ዝክር የምትዘክሩ ተሳስታችኋል፤ ዋናውን ኢየሱስን ዘንግታችኋል” በማለት በተዋሕዶ እምነታችን እያላገጠ የምእመናንን ሞራል ከመንካቱም በላይ የቤተ ክርስቲያናችንን አስተምህሮ እያፋለሰ ሰብኳል፡፡
በዚኹ ጉባኤ፣ በዕለቱ አሸናፊ ገብረ ማርያም ቅዳሴ እንዲቀድስ በማድረግ በጉባኤው ላይም፣ ዓይኑን ጨፍኖ እየዘመረ፣ ክብር ለጌታ ኢየሱስ ይኹን፤ እያለ ሙሉ በሙሉ የመናፍቃኑን እንቅስቃሴ በተዋሕዶ መድረክ እንዲያሳይ አመቻችተዋል፡፡
በሆሳዕና ደብረ ምሕረት ቅዱስ በዓለ ወልድ ቤተ ክርስቲያን፣ በ2008 ዓ.ም. የታኅሣሥ ገብርኤልን ዓመታዊ ክብረ በዓል ምክንያት በማድረግ በተዘጋጀው ጉባኤ በአባ ቢንያም የተጋበዙት መምህራን፣ በገና ጾም፣ “ሥጋ ቤት ውሰዱን” በማለት ከደብሩ ዲያቆናት ጋር ተሟግተዋል፤ የጾም ወቅት ነው ቢባሉም፣ “እኛን አይመለከተንም፤ ሥጋ ቤቱን አሳዩን” በማለት ወደ ምግብ ቤት በመሔድ የፍስክ ምግብ በልተው ተመልሰው በመምጣት ኑፋቄአቸውን ሲነዙ ቆይተው ሲመለሱ፣ አባ ቢንያምም፣ እንደተለመደው አሞክሽተዋቸው ጉባኤው ዘግተዋል፡፡
አባ ቢንያም የስብከተ ወንጌል ተስጥኦ ይኹን ዕውቀት የላቸውም፡፡ በዐውደ ምሕረት ላይ ግን ለረጅም ሰዓት ስለ ራሳቸው ታላቅነትና ልዕልና እያወሩ፣ ፍጹም የበቀልና ዓለማዊ መልእክቶችን ያስተላልፋሉ፡፡ ምእመናንን የሚያሳፍር ቧልት የሚያዘወትሩና ከአባት የማይጠበቅ ስሜታዊነት የሚታይባቸው ናቸው፡፡
በ2006 ዓ.ም. መስከረም 26 ቀን፣ ጋብቻውን በሥርዓተ ተክሊል የፈጸመው የቤተ ክርስቲያን ልጅ ዲያቆን ብርሃኑ አያሌው፣ ጋብቻውን ለመፈጸም ሁለት ቀን ሲቀረው ወደ ሀገረ ስብከት ቢሯቸው ድረስ አስጠርተው አላስፈላጊና አስገዳጅ ጥያቄዎችን በቃልና በጽሑፍ አቅርበውለታል፡፡ በጽሑፍ ባቀረቡት ላይ ወንጀለኛ ነኝ ስትል ካልፈረምክ በማለት ከሕጉና ሥርዓቱ ውጭ ግፊት አድርገውበታል፡፡ ዲያቆን ብርሃኑና የንስሐ አባቱ፣ አንፈርምም በማለታቸው፣ ሥልጣናቸውን አላግባብ በመጠቀም፣ የጋብቻው ዝግጅት ከተጠናቀቀ በኋላ በሀገረ ስብከቱ በየትኛውም አጥቢያ ሥርዓተ ተክሊሉን ለመፈጸም እንዳይችል አድርገዋል፡፡
ግብረ ምንኵስናን በተመለከተ፡-
የምንኵስና ልብሳቸውን አውልቀው ለአንድ መነኵሴ በማይመጥን አኳኋን በኮትና በሱሬ የዘወትር ልብስ በማድረግ በከተማዋ እንደማንኛውም ሰው ይዘዋወራሉ፤
በሰባቱ የቤተ ክርስቲያናችን የዐዋጅ አጽዋማት፣ በተለይ በገናና እና በሰኔ አጽዋማት፣ ሆቴል ገብተው በሕዝብ መካከል ተመልካችን በሚያሳፍርና በሚያሸማቅቅ መልኩ የፍሥክ ምግቦችን በማዘዝ ይበላሉ፤ በይበልጥ ደግሞ በዐቢይ ጾም፣ ለተከታታይ ቀናት በጠዋት ሆቴል እየገቡ የጾም ምግብ በመመገብ፣ አልኮል በመጠጣት አጽዋማትን እየሻሩ የማሰናከያ አለት መኾናቸው፤ በሠርክም ለምእመናን ጉባኤ ከመትጋት ይልቅ ወደ መጠጥ ቤት መሔድን ያዘወትራሉ፤
ከሰዎች ጋር ዓምባጓሮ መፍጠር፤ በተፈጠረ ቁጥር ቆባቸውንና ልብሳቸውን በማሳየት፣ “ይህ አደንዛዥ ዕፅ(ምንኵስና) ይዞኝ እንጂ እያንዳንዳችኹን በጫማ ጥፊ ነበር የምዘረጋችኹ፤” በማለት በዐደባባይ የሚናገሩና ምንኵስናን እንደጸጋ ሳይኾን እንደሸክም የሚቆጥሩ ናቸው፤
ከተለያዩ ሴቶች ጋር ባልተለመዱና ለክርስቲያናዊ አገልግሎት በማይመቹ ሰዓቶችና በድብቅ ቦታዎች በተደጋጋሚ መታየታቸው በምእመኑ ዘንድ በግልጽ የሚታወቅ ጉዳይ ነው፡፡ ቅርበት ባላቸውና በምግባር ይመስሉኛል ብለው ላሰቧቸው ሰዎችም፣ ሚስት ማግባትና ልጅ መውለድ እንደሚፈልጉ በተደጋጋሚ ሲናገሩ ተደምጠዋል፡፡ ሚስት ማግባቱ ባይሳካላቸው እንኳ ልጅ መውለዱ የማይቀር ጉዳይ መኾኑን የውስጣቸውን መስክረዋል፤ “ልጅ ሳልወልድ አልሞትም” ሲሉም ይፎክራሉ፡፡
“ሕዝብ ይወግረኛል ብዬ እንጂ ውዳሴ ማርያም፣ ገድላት፣ ስግደት፣ ጾም፣ ፍትሐት፣ ንስሐ… አስፈላጊ አይደሉም፤” በማለት ተናግረዋል፡፡
በቅዳሴ ሰዓት መቅደስ ውስጥ ተቀመጠው እጅግ የሚዘገንኑና ጸያፍ ፊልሞችን በሞባይል እየጎረጎሩ መመልከት፣ ስልክ ማናገር፣ በፌስቡክ ቻት ማድረግ ቋሚ ሥራቸው ነው፡፡
አስተዳደራዊ የማስፈጸም ብቃትን በተመለከተ፡-
በሆሳዕና ከተማ ጎርጎዴ የሚባለው ሰፈርና የመምህራን ኮሌጅ፣ በተለምዶ ቲቲሲ የሚባለው አካባቢ ምንም ዓይነት ቤተ ክርስቲያን የሌለና ከተማው ውስጥ ከሚገኙ አብያተ መቃድስ ከአራት ኪሎ ሜትር የሚርቅ አካባቢ በመኾኑ፣ ችግሩን የተረዱ የቤተ ክርስቲያን ልጆች፣ የግል ይዞታቸውንና የሌሎች ሰዎችን ይዞታ በማካተት፣ ከ6ሺሕ ካ.ሜ. በላይ የከተማ ቦታ ለሕንፃ ቤተ ክርስቲያን መሥርያነት እንዲውል፤ በሀገረ ስብከቱና በመሬቱ ባለይዞታዎች መካከል የሀገረ ስብከቱ የክፍል ሓላፊዎች በተገኙበት ውል ተፈጽሟል፤ ውሉን ያፈረሰ ወገን ለመንግሥት 50ሺሕ ብር መቀጮ ገደብ ተቀምጧል፡፡
ይኹን እንጂ መሬቱ ምንም ሳይፈይድ ቀርቷል፡፡ የተቀበሉትን መሬት ወደሚመለከተው አካል ይዞ በመሔድ የቤተ ክርስቲያኒቱ እንዲኾን ባለማድረጋቸውና ተገቢውን ባለሟሟላታቸው፣ ለዐሥር ወራት በኋላ በባለቤት አልባነት በመቆየቱ አስተዳደሩ ለሌላ አገልግሎት አውሎታል፡፡ የቀድሞ ባለይዞታዎች ይህን ሰምተው ቢጠይቋቸው፣ ማረጋገጫው እንደጠፋባቸውና ጉዳዩንም እንደረሱት በግዴለሽነት ገልጸውላቸዋል፡፡ በአንፃሩ ለራሳቸው መሬት እየገዙ የሚሸጡና ለሌሎችም እንደ ደላላ ለማግባባት የሚሞክሩ በመኾናቸው ለቤተ ክርስቲያን ዕድገትና ልማት የሚጨነቁ አይደሉም፡፡
ምእመኑ የልማት ጥያቄ ሲጠይቅና አስተያየት ሲሰጥ፣ አስተባብረውና ልዩነቱን አጥብበው ወደ አንድ መንገድ ማምጣት ሲገባቸው፤ የቤተ ክርስቲያን ብቻ የኾነውን ጉዳይ በቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅርና አሠራር መጨረስ ሲገባቸው፤ አግባብነት የሌላቸውን ደብዳቤዎች በማብረርና ለመንግሥት አካል በር በመክፈት በምእመኑና በመንግሥት መካከል ቅራኔ ፈጥረዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያን አላዋቂና ኹሉ የሚሳለቅባት እንድትኾን አድርገዋል፡፡
ሀገረ ስብከቱን ለማስተዳደር ተስኖአቸው በምክትል ሥራ አስኪያጅ ድጋፍ እየተደረገላቸው የሚንቀሳቀሱና ከቃለ ዐዋዲው ውጭ እየመሩ ያሉ መኾናቸው፣ ለአቅመ ቢስነታቸው ማስረጃ ነው፡፡
በሀገረ ስብከቱና አጎራባች አህጉረ ስብከት፣ በቀደሙት ዘመናት ከ67 በመቶ በላይ የነበረው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ቁጥር እጅግ አስደንጋጭ በኾነ መልኩ ወደ 6.3 በመቶ መውረዱን ስታቲስቲካዊ መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ በውድቀት ውስጥ ያለና ሁሉም ሊታደጉት የሚገባ ሀገረ ስብከት በመኾኑ በዚኽ ዓይነቱ የፈተና ወቅት በአባ ቢንያም መንቾሮ ሊመራ አይገባውም፡፡
በአጠቃላይ አባ ቢንያም መንቾሮ፣ ከብዙ በጥቂቱ ከላይ በተጠቀሱ፣ የአስተዳደር ብቃት ውስንነት፤ ለክርስትና እምነት ያላቸው የወረደ አመለካከት፤ በምንኵስና ሕይወታቸው ከመጽናት ይልቅ ልጅ ወልዶ ለመሳም ዘወትር መዛታቸው፤ በኑፋቄው ማዕበል እየተመቱ ያሉና በውስጥ አርበኝነት ያላቸውን ሚና ስንመለከት፤ እርሳቸው ተሸመው ቢመጡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከባድ ኪሳራ እንደሚጠብቃት በቀላሉ መገንዘብ ይቻላል፡፡
ምእመኑ፣ በሐዲያና ስልጤ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ላይ፣ በኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ ደንብ መሠረት አቤቱታውን በአግባቡ ለአስመራጭ ኮሚቴው በማቅረብ ሃይማኖታዊ ግዴታውን የተወጣ በመኾኑ፤ በቅዱስ ሲኖዶስ የተሠየመው አስመራጭ ኮሚቴም፤ ከወገንተኛነት የጸዳና ከትውልድ ተወቃሽነት የሚድንበት ምርጫ በማካሔድ፣ የበግ ለምድ የለበሱ ተኩላዎችን ከጥቆማ እንዲያስወጣ፤ ሕፀፆቻቸውንና ክፍተቶቻቸውን በቅዱስ ሲኖዶስ ደረጃ አጣርቶ በቀኖና ቤተ ክርስቲያንና በሕገ ቤተ ክርስቲያን ተጠያቂ እንዲያደርጋቸው በቤተ ክርስቲያን ስም እንማፀናለን፤ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ምርጫውን እንጸልያለን፡፡
የአባቶቻችን አምላክ፣ ቤተ ክርስቲያናችንን ከፈተና ይሰውርልን፡፡ አሜን፡፡
