የወልቃይት ኮሚቴ አባል ታሠሩ:: VOA Amharic
አቶ ባየኝ የተያዙት ከጎንደር ወደ ሚኖሩበት ቀበሌ እየተጓዙ ሣሉ ዳንሻ ከተማ ከመግባታቸው በፊት ባለው መከዞ የሚባል ኬላ ላይ መሆኑን የኮሚቴው አባል የነበሩት አቶ አታላይ ዛፌ ለቪኦኤ ገልፀዋል።
ቀደም ሲልም የአቶ ባየው የአራት ዓመት ልጅ ተጠልፎ እንደነበረ የገለፁት አቶ አታላይ በሌሎችም የኮሚቴው አባላት ላይ ማስፈራሪያና ዛቻ እንደሚሰማ፤ የማይ ካድራ ነዋሪ የሆኑት አቶ ፀጋዬ ውብነህ የሚባሉ የኮሚቴው አባል የሆኑ ሰው በሌሊት በደረሣቸው ማስፈራሪያ ከሚኖሩበት መፈናቀላቸውን፤ አቶ መብራህቴ ታከለ የሚባሉ ሰው በአንድ የቀበሌ ሊቀመንበር በጠርሙስ ፊታቸው ላይ መመታታቸውንና ሌሎችም የወከባ አጋጣሚዎችን ዘርዝረው አስረድተዋል።
ቀደም ሲል ወደ ፌደሬሽን ምክር ቤት የገባውን ፊርማ የፈረሙ ሰዎች በፖሊስና ሲቪል በለበሱ ሰዎች እየተጠሩ ወይም ወደ ፖሊስ ጣቢያ እየተወሰዱ ማስፈራሪያና ዛቻ እንደሚደርስባቸው፤ “… በነጭ ወረቀት ላይ ወይም አበል ተቀበሉ ተብለው መልዕክቱን በማያውቁት ወረቀት ላይ ወይም አሳስተው ነው ያስፈረሙን እያሉ…” እንዲፈርሙ እንደሚደረጉ በተለያዩ አጋጣሚዎች ለቪኦኤ ተናግረዋል።
የአካባቢውን ባለሥልጣናት ለማግኘት ብዙ ጥረት እያደረግን ነው።
ከአቶ አታላይ ዛፌ ጋር ለተደረገው ሙሉ ቃለ-ምልልስ የተያያዘውን የድምፅ ፋይል ያዳምጡ።
http://amharic.voanews.com/emailtofriend/audio/Audio/3204358.html?isflashembed=true
