የቢዝነስ ስልኮች ፦ክቡር ሚኒስትሩ አንድ ትልቅ ሆቴል ውስጥ የቀጠሩት ደላላ አረፈደባቸው::

[ክቡር ሚኒስትሩ አንድ ትልቅ ሆቴል ውስጥ የቀጠሩት ደላላ ስላረፈደባቸው ደወሉለት]
–    ሄሎ ክቡር ሚኒስትር፡፡
–    የት ደርሰሃል?
–    ኧረ ክቡር ሚኒስትር ታስሬያለሁ፡፡
–    ማን አሰረህ?
–    ማለቴ መንገዱ ተዘጋግቶ አንድ ቦታ ታስሬያለሁ፡፡
–    ለምንድን ነው መንገድ የተዘጋው?
–    ስብሰባ አለ ነው የሚሉት፡፡
–    የምን ስብሰባ?
–    የአፍሪካ ኅብረት ነው ምናምን አሉ፡፡
–    ታዲያ ሌላ አማራጭ መንገድ አትጠቀምም?
–    ወይ አማራጭ መንገድ?
–    ምነው?
–    ሁሉም መንገድ ተዘጋግቷል ስልዎት፡፡
–    ኪራይ ሰብሳቢ ነህ ልበል?
–    ምነው ክቡር ሚኒስትር?
–    እንዴት ምንም መንገድ የለም ትላለህ?
–    የለማ ታዲያ ምን ላድርግ?
–    ለዚህ እኮ ነው ኪራይ ሰብሳቢ ነህ ያልኩት፡፡
–    እንዴት ክቡር ሚኒስትር?
–    ሰፈር ውስጥ ሳይቀረን አይደል እንዴ መንገድ የሠራነው?
–    ምን አሉኝ?
–    እንደ ሠንሠለት የተያያዘ መንገድ አይደል እንዴ የሠራነው፡፡
–    አይ ክቡር ሚኒስትር፡፡
–    እና አልደርስም እያልከኝ ነው?
–    ይቅርታ ክቡር ሚኒስትር፡፡
–    ምን ዓይነት ጣጣ ነው?
–    ለምንድን ነበር የፈለጉኝ?
–    ለጥብቅ ጉዳይ ነዋ፡፡
–    በስልክ አይነግሩኝም?
–    በስልክ የሚነገር አይደለም፡፡
–    ለዛሬ ቢነግሩኝም ግን ችግር የለውም፡፡
–    ለምንድን ነው ችግር የሌለው?
–    ያው ቢግ ብራዘሮች በከተማዋ ትልቅ ስብሰባ ስላለ በዛ ስለሚጠመዱ እኛ ትዝ አንላቸውም ብዬ ነው፡፡
–    ፈልጌ ነበር፡፡
–    ምንድን ነው የፈለጉት?
–    ዶላር ነዋ፡፡
–    ይጠይቁዋ ታዲያ?
–    የት ነው የምጠይቀው?
–    ባንክ ነዋ፡፡
–    ቀልዱን ለምን አትተውም?
–    ክቡር ሚኒስትር ሰሞኑን እኮ ቅጥል ነው ያደረጋችሁን፡፡
–    ለምንድን ነው የተቃጠላችሁት?
–    በቃ ዶላር ሰውን አንበሽብሻችሁት እኛ ጋ እኮ ወደቀ፡፡
–    ያጋጥማል እንግዲህ፡፡
–    ክቡር ሚኒስትር ክፉኛ እኮ ነው የከሰርኩት፡፡
–    ስንት ከሰርክ?
–    ኧረ አልጠራው ቁጥሩን፡፡
–    ለምን?
–    ስጠራው ያመኛል፡፡
–    አስፕሪን መዋጥ ነዋ፡፡
–    አስፕሪን የሚያሽለው ቁጥር አይደለም፡፡
–    ለማንኛውም በአስቸኳይ ፈልግልኝ፡፡
–    ምን ያህል?
–    የቻልከውን ያህል፡፡
–    መቼም እኔ ለእርስዎ የማልሆነው ነገር የለም?
–    እኔስ ለአንተ የማልሆነው ምን አለ?
–    ድር ቢያብር …
–    ዶላር ያስር!
[ክቡር ሚኒስትሩ ለምሳ ቤት ሲሄዱ ሚስታቸውን አገኟቸው]
–    እኔ የምልሽ?
–    ምንድን ነው?
–    የአንቺ ቢዝነሶች መቼ ነው የሚያተርፉት?
–    ምን ለማለት ፈልገህ ነው?
–    ባለፈው ማተሚያ ቤት ክፈትልኝ አልሽ ከፈትኩልሽ፡፡
–    እናሳ?
–    ከዛም በኋላ ሞባይል ቤት አልሽ እሱም ተከፈተ፡፡
–    ልክ ነው፡፡
–    ትርፍ ግን ሲያመጡ አላይም፡፡
–    እንዴት ማለት?
–    ቢያተርፉ ኖሮማ እስኪብርቶ እንኳን ትገዥልኝ ነበር፡፡
–    እኔ እኮ ከእስኪብርቶ ፋብሪካው ይሻላል ብዬ ነው፡፡
–    የምን ፋብሪካ?
–    የእስኪብርቶ ፋብሪካ ነዋ፡፡
–    ትቀልጃለሽ?
–    የምን ቀልድ ነው፤ መንግሥት ራሱ ወደ ኢንዱስትሪ ግቡ እያለ አይደል?
–    እሺ የእኛ የኢኮኖሚ ተንታኝ፡፡
–    ተሳሳትኩ እንዴ?
–    ስሚ መቼም በከፈትኩልሽ ቢዝነሶች ከብዙ ሰዎች ጋር ትገናኛለሽ ብዬ አስባለሁ?
–    አዎን ምነው?
–    እስኪ አፈላልጊልኝ፡፡
–    ምንድን ነው የማፈላልግልህ?
–    ዶላር ነዋ፡፡
–    ምን ያህል?
–    ቁጥሩን ቴክስት አደርግልሻለሁ፡፡
–    ዶላር ስትል እኔንም አስታወስከኝ፡፡
–    ምንድን ነው ያስታወስኩሽ?
–    እኔም እፈልጋለሁ፡፡
–    ምን?
–    ዶላር ነዋ፡፡
–    ለምን?
–    አሜሪካ ያለችው ልጃችን ምርቃት እኮ ደርሷል፡፡
–    ወይ ጣጣ፡፡
–    ሲሆን አንተም መምጣት አለብህ፡፡
–    አገሪቷን ለማን ትቼ?
–    ስለዚህ እኔ ከእህቴ ጋር እሄዳለሁ፡፡
–    ስለዚህ?
–    ያው ለሁለታችንም የሚበቃ ዶላር ፈልግልና፡፡
–    ወይ ጣጣ፡፡
–    ከዛም ልጅህን ትንሽ ማዝናናት አለብኝ፡፡
–    ምን ዓይነት ነገር ነው?
–    እንድታስብበት ብዬ ነው፡፡
–    ምኑን?
–    ዶላሩን!
[ለክቡር ሚኒስትሩ አንድ ዳያስፖራ ደወለላቸው]
–    ሄሎ!
–    ምነው ክቡር ሚኒስትር?
–    ምነው?
–    የተበሳጩ ይመስላሉ፡፡
–    ምን ባክህ አስቸጋሪ ሆነ እኮ?
–    ምኑ?
–    ዶላር ማግኘት፡፡
–    ይኸው ሰሞኑን እንዳንበሻበሻችሁት ሰምቼ አይደል እንዴ!
–    እኛ አልተንበሻበሽንማ፡፡
–    ለራስዎት ነው እንዴ የፈለጉት?
–    አዎን፡፡
–    ለምን አልክልዎትም እኔ ታዲያ?
–    አንተ ብትልክልኝም እዚህ የሚደርሰኝ በብር ነው፡፡
–    እሱስ ልክ ነው፡፡
–    ሲቀጥል የምፈልገው መጠን ደግሞ አንተ የምትችለው አይደለም፡፡
–    ይኼን ያህል?
–    አገሪቷ እኮ አድጋለች፡፡
–    እርስዎም አድገዋል እንጂ፡፡
[ክቡር ሚኒስትሩ አማካሪያቸውን አስጠሩት]
–    መቼም የግል ሚዲያ ትከታተላለህ?
–    አዎን ክቡር ሚኒስትር፣ እርስዎም ቢከታተሉ ጥሩ ነው፡፡
–    አንተን የቀጠርኩህ ተከታትለህ ሪፖርት እንድታደርግ መስሎኝ?
–    አይ እንዲሁ ነገሩን ነው፡፡
–    ለመሆኑ ሰው ዶላር ከየት ነው የሚያገኘው?
–    ያው ከባንክ ነዋ፡፡
–    ከዚያ ሌላ?
–    ከብላክ ማርኬት ነዋ፡፡
–    ከእሱ ሌላ?
–    ከሰሞኑ ስብሰባ ነዋ፡፡
–    ቀልዱን ተው እስቲ፡፡
–    ማለቴ ለአፍሪካ ኅብረት ስብሰባ ከሚመጡት ተሰብሳቢዎች ማለቴ ነው፡፡
–    እንዴት ማለት?
–    ያው ተሳታፊዎቹ ዶላር ይዘው ስለሚመጡ ከእነሱ ሊገኝ ይችላል፡፡
–    የት ነው የሚገኙት እነሱ?
–    ሆቴላቸው ነዋ፡፡
[ክቡር ሚኒስትሩ አንድ ባለሆቴል ወዳጃቸው ጋ ደወሉ]
–    ጤና ይስጥልኝ ክቡር ሚኒስትር፡፡
–    እንዴት ነህ ባክህ?
–    ዛሬ ከየት ተገኙ?
–    ሁሌም እኔ ነኝ እንጂ አንተ መቼ ትፈልገኛለህ?
–    አይ ክቡር ሚኒስትር እርስዎም ጉዳይ ሲኖርዎት ነው የሚፈልጉኝ፡፡
–    እ…
–    ምን ልታዘዝ ታዲያ?
–    ሥራ እንዴት ነው?
–    ያው ከእጅ ወደ አፍ ነው፡፡
–    የሆቴል ሥራውን ማለቴ ነው፡፡
–    ምንም አይል፡፡
–    ሰሞኑን እንግዶቹ እየመጡ ነው?
–    አዎ ሰሞኑን እንኳን ቢዚ ሆነናል፡፡
–    አንድ ነገር ላስቸግርህ ነበር፡፡
–    ምን ክቡር ሚኒስትር?
–    ለአክስቴ ልጅ እናንተ ሪሰፕሽን ጋ ትንሽ ሱቅ ፈልጌ ነበር፡፡
–    የምን ሱቅ?
–    የዶላር መመንዘሪያ፡፡
–    እሱ ሥራ እኮ የመንግሥት ፈቃድ ያለው ባንክ ብቻ ነው የሚሠራው፡፡
–    ስለእሱ አታስብ፡፡
–    እንዴት አላስብ ክቡር ሚኒስትር፡፡
–    እኔ ሁሉን ነገር እጨርሰዋለሁ፡፡
–    ይጠንቀቁ ግን፡፡
–    ምኑን?
–    እጨርሳለሁ ብለው እንዳይጨረሱ!
[ክቡር ሚኒስትሩ ቤት ሲገቡ ሚስታቸውን አገኟቸው]
–    እኔ የምልህ?
–    ምንድን ነው?
–    ዶላሩን የምትፈልገው ለምንድን ነው?
–    ለጨረታ፡፡
–    የምን ጨረታ?
–    ከአንድ የውጭ ኩባንያ ጋር ልሠራው ያሰብኩት ሥራ አለ፡፡
–    ሥራ ቀየርክ እንዴ?
–    የምን ሥራ?
–    ሚኒስትርነትህን፡፡
–    ወደ ምንድን ነው የምቀይረው?
–    ወደ ኢንቨስተርነት፡፡
–    ምን?
–    ጡረታዬ እየደረሰ እንደሆነ አትርሺ፡፡
–    ለመሆኑ ተሳካልህ?
–    ምኑ?
–    የዶላሩ ፍለጋ፡፡
–    ኧረ ተይኝ እስቲ፡፡
–    ምነው?
–    ምንም የሚያበረታታ ነገር አይደለም፡፡
–    ለመሆኑ የት ነው የፈለግከው?
–    ያልፈለግኩበትን ጠይቂኝ፡፡
–    እኮ የት የት ፈልገሃል?
–    ከአባ ኮራን ሰፈር …
–    እ…
–    እስከ አባ ኮራፕት ሰፈር! === http://www.ethiopianreporter.com/