ለኩላሊት ሕመምተኞች የተሰበሰበው ገንዘብ… እያወዛገበ ነው

    በቅርቡ የተቋቋመው የኩላሊት እጥበት ማዕከል፣ ለኩላሊት ሕመምተኞች የእጥበት ህክምና ለመስጠት በኤስ ኤም ኤስ እያሰባሰበ ያለው ገንዘብ፣ “ለታለመለት ዓላማ አልዋለም”፤ መባሉ እያወዛገበ ነው፡፡ ባለፈው አርብ ጥቅምት 26 ሬዲዮ ፋና ባስተላለፈው ዘገባ፣ ማዕከሉ ለኩላሊት ህመምተኞች የእጥበት አገልግሎት ለመስጠት ከህዝብ ከሚሰበሰበው የበጐ አድራጐት ገቢ፣ ኮሚሽን እየከፈለ መሆኑን ጠቅሶ ድርጊቱ ህገወጥ ነው ብሏል፡፡ 524 ሺህ ብር ኮሚሽን ተቀብያለሁ ያሉ ግለሰብም በዋቢነት ማቅረቧ ታውቋል፡፡ የማዕከሉ የቦርድ አባልና የገቢ አሰባሳቢ ኦፊሰር ደራሲና ዳይሬክተር አንተነህ ሃይሌ በበኩሉ፤ “የኩላሊት እጥበት ማዕከሉ በSMS ከህዝብ ከሰበሰበው 7 ሚሊዮን ብር ውስጥ 4 ሚሊዮን ብር ተመዝብሯል የሚል ዘገባ በሬዲዮ ፋና መሰራጨቱን ጠቁሞ፤ 7 ሚ. ብር የሚለውን ከየት አምጥቶ እንዳወራ አናውቅም ብሏል፡፡ “የፋና ሃሰተኛ ዘገባ የህዝቡን በጐነት የሚረብሽና የህሙማንን ህልም የሚያጨልም ነው፤” ሲልም ተችቷል፡፡“የፋና ዘገባ እውነትን ማዕከል ያደረገ አይደለም፤” ያሉት የማዕከሉ የቦርድ ሰብሳቢ ኢንጂነር ሳሙኤል ይርጋ፤ “ለሚሠራው ሥራ የሚከፈል ኮሚሽን የለም” ሲሉ አስተባብለዋል፡፡ማዕከሉ ከገራዶ ፊልም ፕሮዳክሽን ጋር ስለፈጸመው የሥራ ውል የተጠየቁት ሰብሳቢው፣ “ማዕከሉ ሥራ ሲጀምር ምንም ገንዘብና የሰው ሃይል ስላልነበረው የኤስኤምኤሱን አጠቃላይ ሥራ እንዲያከናውንና ለእድለኞች ሽልማት ከገቢው ከ10 በመቶ ያልበለጠ ሒሳብ እንዲወራረድለት ውል ፈጽመናል” ብለዋል፡፡ እያንዳንዱም ወጪ በደረሰኝ እንደሚገባና እንደሚወጣ ከቀሪው ጋር የሚያሳይ የባንክ ስቴትመንት እንዳለ ገልፀዋል፡፡ ሬዲዮ ፋና ያለ መረጃ ያሰራጨውን ዜና በተመለከተ፣ ይቅርታ እንዲጠይቀን ደብዳቤ አስገብተናል – ብለዋል ሰብሳቢው፡፡