ቅ/ሲኖዶስ: በ“ፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ” እና በሙስና ጉዳዮች ውሳኔ ይሰጣል፤ላልተተገበሩ ውሳኔዎቹ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ያቋቋማል
- በቤተ ክርስቲያን ስም በሚዲያዎች ስለሚተላለፉ ‘ትምህርቶች’ ይወስናል
- የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አስተዳደር ጉዳይ ከመነጋገርያ አጀንዳዎቹ ተካቷል
- እነየማነ ዘመንፈስ ቅዱስ፣ በአዳራሹ መግቢያና በአባቶች ቤት ደጅ እየጠኑ ነው
በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቁጥር 164 ድንጋጌ መሠረት፣ ትላንት ጥቅምት 12 ቀን በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ የመክፈቻ ንግግር የተጀመረው የቅዱስ ሲኖዶስ ዓመታዊ መደበኛ ስብሰባ፤ ዘመኑን የዋጁ እና ወቅቱን የተመለከቱ የመነጋገርያ አጀንዳዎችን በማጽደቅ ውይይቱን ቀጥሏል፡፡
ምልአተ ጉባኤው በትላንት የመጀመሪያ ቀን ውሎው፣ የመነጋገርያ አጀንዳዎቹን አርቅቀው እንዲያቀርቡ ስድስት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የሚገኙበት ኮሚቴ ሠይሟል፡፡ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስን በሰብሳቢነት፣ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤልን በጸሐፊነት፣ የቅዱስ ሲኖዱሱን ዋና ጸሐፊ ብፁዕ አቡነ ሉቃስን በአስረጅነት የያዘው ኮሚቴው፣ ቀደም ሲል በቋሚ ሲኖዶስ ተቀርጸው ለምልአተ ጉባኤው በተዘጋጁ አጀንዳዎች ላይ በስፋት መክሮ፣ ዘመኑን የዋጁና ወቅቱን የተመለከቱ ኾነው ከዳበሩ በኋላ ለምልአተ ጉባኤው ቀርበው እንዲጸድቁ ተደርጓል፡፡
የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ኹኔታ በጥልቀት ለማየት እንደሚያስችሉ ከታመነባቸው 26 የመነጋገርያ አጀንዳዎች ውስጥ፤ የመልካም አስተዳደር ዕጦትን፣ የሙስና መስፋፋትን፣ የሚተላለፉ ውሳኔዎች አስፈጻሚ ማጣትን፤ የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ እንቅስቃሴንና ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን የተመለከቱ ዐበይት ጉዳዮች እንደሚገኙበት ለማወቅ ተችሏል፡፡
(አዲስ አድማስ፤ ቅጽ ፲፮ ቁጥር ፰፻፳፫፤ ቅዳሜ ጥቅምት ፲፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም.)
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ፣ የቤተ ክርስቲያንን ቀጣይ ህልውና እየተፈታተኑና የምእመናኗን ፍልሰት እያባባሱ ባሉ፤ የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ እና የመልካም አስተዳደር ጉዳዮች ላይ በጥልቀት በመምከር ውሳኔ እንደሚያሳልፍ ተገለጸ፡፡
የቅዱስ ሲኖዶሱ የመጀመሪያ ዓመታዊ መደበኛ ስብሰባ፣ ከትላንት በስቲያ በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም በመክፈቻ ጸሎት ሥነ ሥርዐት የተጀመረ ሲኾን በምልአተ ጉባኤ የተሠየመው አጀንዳ አርቃቂ ኮሚቴ በቀረፃቸውና በምልአተ ጉባኤው በጸደቁ የመነጋገርያ ነጥቦች ለቀናት እንደሚመክር ታውቋል፡፡
የቅዱስ ሲኖዶሱን ዋና ጸሐፊ በአስረጅነት ያካተተውና ስድስት ሊቃነ ጳጳሳትን የያዘው አርቃቂ ኮሚቴ፣ ለምልአተ ጉባኤው ካቀረባቸው ከ26 ያላነሱ አጀንዳዎች መካከል፤ በቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅር ሰርገው በመግባት አስተምህሮዋን፣ ሥርዐቷንና ትውፊቷን ውስጥ ለውስጥ በመበረዝ ጉዳት እያስከተሉያሉየፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ አራማጆች ጉዳይ አንዱ ሲኾን የእንቅስቃሴውን ችግር የተመለከቱ ጥናቶች እና መረጃዎች በጥልቀት ይፈተሹበታል፡፡
ከቅዱስ ሲኖዶሱ ስብሰባ ቀደም ብሎ፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ደረጃ ለ34ኛ ጊዜ የተካሔደው የሰበካ አስተዳደር አጠቃላይ ጉባኤ ባወጣው መግለጫ፤ በቤተ ክርስቲያን የተወገዘውን የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄን ተጽዕኖ ለመቋቋምና የምእመናንን ፍልሰት ለመግታት በቂና መጠነ ሰፊ በኾነ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ምእመናንን በእምነታቸው ለማጽናት የጋራ አቋም ተይዟል፤ ለተፈጻሚነቱም በልዩ ልዩ ብሔረሰቦችና ቋንቋዎች የሚያስተምሩ መምህራንን በጥራትና በቁጥር ማሳደግ፤ ማሠልጠኛዎችንና ኮሌጆችን በየአህጉረ ስብከቱ ማቋቋም፤ የነባሮቹን ምልመላ፣ ቅበላና ሥርዐተ ትምህርት መፈተሽ፤ እንዲኹም የስብከተ ወንጌል አገልግሎቱን ዘመኑ በሚፈቅዳቸው ሚዲያዎች በመታገዝ ለመላው ዓለም ማዳረስ ትኩረት ተሰጥቷቸዋል፡፡
ሚዲያዎቹ፣ ቤተ ክርስቲያን የራስዋን ድምፅ የምታሰማባቸው እና ማእከላዊነታቸውን የጠበቁ መኾን እንደሚገባቸው በመግለጫው የተጠቀሰ ሲኾን ቅዱስ ሲኖዶሱም በቤተ ክርስቲያን ስም በልዩ ልዩ ሚዲያዎች በመተላለፍ ላይ ስለሚገኙ ‘ትምህርቶች’ ከምእመናን ሲቀርቡ የቆዩ አቤቱታዎችን በአጀንዳው በማካተት ቀደም ሲል ባጸደቀው የሚዲያ ጥናት መሠረት ውሳኔ እንደሚያሳልፍ ተጠቁሟል፡፡
የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ አራማጆች፤ አስተምህሮዋን ከመፃረር ባሻገር በአንዳንድ የሀገር ውስጥ እና የውጭ አካባቢዎች፣ ማእከላዊውን አስተዳደሯን የሚፈታተን “ገለልተኛ አስተዳደር” በመፍጠር ምእመናኗን እያደናገሩ እንደሚገኙ ተመልክቷል፡፡ የመልካም አስተዳደር ዕጦት እና ሙስና ለችግሩ አስተዋፅኦ እንዳለው በጋራ አቋሙ የገለጸው አጠቃላይ ጉባኤው፣ ለቤተ ክርስቲያኒቱ የወደፊት ህልውና ከፍተኛ ስጋት በመኾኑ ቅዱስ ሲኖዶሱ መዋቅሯን የሚያጠናከር እና የሕግን የበላይነት የሚያረጋግጥ አስቸኳይ መፍትሔ እንዲፈልግለት ጠይቋል፡፡
ለሙስና እና ብክነት የተጋለጡ አሠራሮችን በወሳኝ መልኩ ለመቅረፍ፣ ከመሪ ዕቅድ ዝግጅት ጀምሮ መዋቅሯ፣ አደረጃጀቷ እና አሠራሯ ዘመኑን በሚዋጅ የግልጽነት፣ የተጠያቂነት እና የአሳታፊነት መርሕ ላይ ለመመሥረት ያስችላሉ የተባሉ ዐበይት ውሳኔዎች በቅዱስ ሲኖዶሱ ሲተላለፉ ቢቆዩም ተግባራዊነት ግን የራቃቸው ኾነዋል፡፡
ያልተተገበሩ ውሳኔዎቹን በመለየት በዝርዝር ይገመግማል የተባለው ምልአተ ጉባኤው፤ ተፈጻሚነታቸውን በመከታተል መዋቅራዊ ለውጡን የሚያረጋግጥ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ሊያቋቋም እንደሚችልና በቀጣይነትም ከኹሉም አካላት የተውጣጣ የቤተ ክርስቲያኗን ኹለንተናዊ ችግር የሚያጠና ኮሚቴ እንደሚሠይም ተጠቁሟል፡፡
በተጨማሪም፤ በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ አንቀጾች የተመለከቱ ደንቦችን፣ ፖሊሲዎችንና አሠራሮችን በተጣጣመ መልኩ የሚያወጣ አካል እንደሚሠየም የተጠቀሰ ሲኾን የፓትርያርኩ ልዩ ሀገረ ስብከት የኾነው የአዲስ አበባ ልዩ መተዳደርያ ደንብ እና ከባድ ቀውስ የፈጠሩት የአስተዳደር ችግሮቹ በአጀንዳነት ተካትቶ እንደሚታይ ተገልጧል፡፡
ይህ በእንዲኽ እንዳለ፣ በአወዛጋቢ ኹኔታ ያገኙትንና የምዝበራ መሣርያ ያደረጉትን ሥልጣናቸውን ለማሰንበት እየተሯሯጡ ያሉት እነ የማነ ዘመንፈስ ቅዱስ፣ ከመክፈቻ ጸሎት ሥነ ሥርዐቱ ምሽት አንሥቶ ቀደም ብለው በጀመሩት አኳኋን በብፁዓን አባቶች ቤት እስከ እኩለ ሌሊት ድረስ ደጅ እየጠኑና እየወተወቱ ናቸው፡፡
በሕገ ወጥ ጥቅም የተቆራኙ የሀገረ ስብከቱ የአስተዳደር ሓላፊዎች፣ “የለውጥ ሒደቱን ማስቀጠል” በሚል ማጭበርበሪያና ሽፋን ተቀናጅተው በተሠማሩበት በዚኽ የደጅ ጥናት እና የውትወታ ዘመቻ፣ ሀገረ ስብከቱ እንዲፈተሽና የእርምት ርምጃ እንዲወሰድ የሚያሳስቡ ብፁዓን አባቶች ትኩረት ተደርጎባቸዋል፡፡ ደጅ ጥናቱ እና ልምምጡ፣ የምልአተ ጉባኤው አባላት ለስብሰባ በሚገቡባቸውና በሚወጡባቸው የአዳራሹ በሮችም ሳይቀር ሰዓት ጠብቆ እየተካሔደ ነው፡፡
የእነ የማነ ዘመንፈስ ቅዱስን በውትወታ የማጨናነቅ አካሔድ ከታዘቡ ብፁዓን አባቶች መካከል፣ “አንድያውን ለምን አብሮን አይሰበሰብም?” በማለት በኹኔታው መሰላቸታቸውንና መገረማቸውን የገለጹ ይገኙበታል፡፡
የመሪ ዕቅድ ጥናቱን ጨምሮ ዓመታዊ በጀትን መወሰን፤ ስለገዳማትና ካህናት ማሠልጠኛ፤ ስለተዘጉ አብያተ ክርስቲያናት፤ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንና በግብጽ ኮፕት ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን መካከል የተደረገውን የፕሮቶኮል ስምምነት መርምሮ የጋራ ኮሚቴ ማቋቋም፤ በጃፓንና በኮርያ አዲስ አብያተ ክርስቲያን ስለማቋቋም በልኡካኑ በቀረበው ጥናት ላይ መወሰን፤ በሕፃናትና ቤተሰብ ጉዳይ ድርጅት ሥር በሚገኙ የቤተ ክርስቲያን ቦታዎች የቀረበውን ጥናት መመልከት፤ የደብረ ጽጌ ገዳም እና የቁሉቢ ደ/ኃ/ቅዱስ ገብርኤል ገዳማት ደንቦች፤ የኢሉባቦር እና ጋምቤላ፣ የኢየሩሳሌም፣ የዋሽንግተን ዲሲ እና ካሊፎርኒያ አህጉረ ስብከት ጉዳዮች፤ ስለኤጴስ ቆጶሳት ምርጫ ጥናት፤ ስለወቅቱ ድርቅ… የመሳሰሉት ከጸደቁት አጀንዳዎች የሚጠቀሱ ናቸው፡፡
