ሰበር ዜና – ሊቀ ካህናት መርዓዊ ተበጀ በአጠቃላይ ሰበካ ጉባኤው ተቃውሞ ከመድረክ ወረዱ፤ “የእግዚአብሔር ሥራ ነው”/ብፁዕ አቡነ ሙሴ/
- “ሦስተኛ ሲኖዶስ አቋቁመዋል” በሚል ብፁዕ ሊቀ ጳጳሱን ለመክሠሥ ተዘጋጅተው ነበር
- “ቤተ ክርስቲያን ለ30 ዓመት በሰላም ኖራ እየተናወጠች ትገኛለች”/ሊቀ ካህናት መርዓዊ ተበጀ/
- “መጥነው እንዲያወሩ ዕድል ቢሰጣቸው ተዋረዱ፤ የእግዚአብሔር ሥራ ነው”/ብፁዕነታቸው/
ከሦስት ዐሥርት ዓመታት በላይ በጀርመን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሓላፊነት ሲያገለግሉ የቆዩትና ከደቡብ ምሥራቅ እና ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት ጋር ውዝግብ ውስጥ የገቡት፣ ሊቀ ካህናት ዶ/ር መርዓዊ ተበጀ፣ በ34ኛው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ መንፈሳዊ ጉባኤ ላይ በገጠማቸው ጠንካራ ተቃውሞ ንግግራቸው ተቋርጦ ከመድረክ ተገፍተው ወረዱ፡፡
ሊቀ ካህናቱ ዶ/ር መርዓዊ የመናገር ዕድል የተሰጣቸው፣ የሀገረ ስብከቱን፣ የደቡብ ምሥራቅ እና ምዕራብ አውሮፓ ዓመታዊ ሪፖርት ቀድመው ለአጠቃላይ ጉባኤው ባሰሙት በሊቀ ጳጳሱ ብፁዕ አቡነ ሙሴ ጋባዥነት ነው፡፡
ሊቀ ካህናቱ፣ በጀርመን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አመሠራረት ሲያብራሩ ከቆዩ በኋላ፣ ከብፁዕ ሊቀ ጳጳሱ ጋር ተፈጥሯል ስለሚሉት ችግር ለማስረዳት ሲጀምሩ ነበር ከአጠቃላይ ጉባኤው በተሰሙ ድምድምታዎች ንግግራቸውን ለማቋረጥ የተገደዱት፡፡
