(ዶክተር?)ዸብረጺሆን ከዲያስፖራው የተጠየቀ ገንዘብ አልተገኘም ::ከመንግስት ሰራተኛው አስገድደው እየመነተፉ እንደሚገኙ ተናግረዋል::
‹‹ትውልደ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያንን ስብሰባ ጠርተን አንዱ 400 ዶላር ወይም አንድ ሺሕ ዶላር ይላል፡፡ ነገር ግን ይህ አካሄድ ሕገወጥ ነው በመባላችን አቁመነዋል፤›› …………… ‹‹አውሮፓ ያለው የገንዘብ መዋጮም ደከም ያለ ነው፤›› (ዶክተር?)ዸብረጺሆን

መንግሥት ከዳያስፖራው በተለይም አሜሪካና አውሮፓ ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ለመሰብሰብ የታሰበውን ያህል የገንዘብ መዋጮ አለማግኘቱን፣ በምክትል ጠቅላይሚኒስትር ማዕረግ የፋይናንስና የኢኮኖሚ ክላስተር አስተባባሪና የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዶ/ር ደብረ ጽዮን ገብረ ሚካኤል አስታወቁ፡፡
‹‹አገር ውስጥ ካሉ ሠራተኞችና ዜጎች የተሰበሰበው የገንዘብ መጠን ከበቂ በላይ ነው፡፡ በተለይ በሠራተኛው በኩል የተለየ ቁርጠኛነት አስተውለናል፤›› በማለት አገር ውስጥ ያለው የገንዘብ አስተዋጽኦ ከፍተኛ እንደሆነ አስታውቀዋል፡፡ ‹‹የውጭ የገንዘብ አስተዋጽኦ የተለያየና ቅልቅል የሚስተዋልበት ነው፡፡ በዋናነት የፍላጎት አይደለም፡፡ ነገር ግን የውጭው የገንዘብ አስተዋጽኦ በአጠቃላይ ጥሩ የሚባል አይደለም፤›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡
ከውጭ የተጠበቀውን ያህል ገንዘብ መሰብሰብ ያልተቻለበት የተለያዩ ምክንያቶች እንዳሉ የገለጹት ዶ/ር ደብረ ጽዮን፣ ‹‹ለምሳሌ አሜሪካ የገጠመን የአሜሪካ መንግሥት ደስተኛ አይደለም፡፡ ምክንያቱም እዚያ አገር ውስጥ የምትከተለው የራሱ ሕግ አለው፡፡ መዋጮ አዋጣ ወይም ቦንድ ግዛ ለማለት የምትከተለው ሕግ አለ፡፡ በቀላሉ የሚሠራ አይደለም፤›› በማለት ባለው የሕግ ክፍተት ምክንያት የታሰበውን ያህል ገንዘብ አለመገኘቱን አብራርተዋል፡፡
‹‹ትውልደ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያንን ስብሰባ ጠርተን አንዱ 400 ዶላር ወይም አንድ ሺሕ ዶላር ይላል፡፡ ነገር ግን ይህ አካሄድ ሕገወጥ ነው በመባላችን አቁመነዋል፤›› ብለዋል፡፡
አሜሪካ ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ብዙ ተጠብቆ እንደነበር የገለጹት ዶ/ር ደብረ ጽዮን፣ ‹‹አሁን ሕጉ በሚፈቅደው መሠረት አጠናክረን ዘንድሮ እንጀምራለን፤›› ብለው፣ የተፈጠረው የሕግ ክፍተት ተሞልቶ በከፍተኛ ሁኔታ ለመንቀሳቀስ ሥራዎች መጠናቀቃቸውን አስረድተዋል፡፡ በተመሳሳይ ‹‹አውሮፓ ያለው የገንዘብ መዋጮም ደከም ያለ ነው፤›› በማለት አክለው አስረድተዋል፡፡
ምንም እንኳን በአሜካሪና በአውሮፓ ለግድቡ የሚደረገው አስተዋጽኦ ከተጠበቀው በታች ቢሆንም፣ በመካከለኛው ምሥራቅ ያሉ ዜጎች በከፍተኛ ሁኔታ ለግድቡ አስተዋጽኦ እንዳበረከቱ ተገልጿል፡፡
‹‹መካከለኛው ምሥራቅ ጥሩ ነው የሄደው፡፡ ተሳትፎውም ሆነ መጠኑ ጥሩ ነው፡፡ አገር ውስጥ ካለው በስሜትም የሚለይ አይደለም፡፡ የሕግ ጉዳይም የለም፤›› በማለት አስረድተዋል፡፡
የተጠበቀውን ያህል ገንዘብ ያልተገኘበት ምክንያት በምንም ዓይነት ሁኔታ ከተቃውሞ ጋር እንደማይገናኝ የገለጹት ዶ/ር ደብረ ጽዮን፣ ‹‹ተቃውሞ ይነሳል አዲስ ነገር አይደለም፡፡ እነርሱ ግን ከዳያስፖራው ማኅበረሰብ አንፃር በጣት የሚቆጠሩ እብዶች ናቸው፡፡ በጣት የሚቆጠሩ እብዶች ደግሞ የትም ቦታ አሉ፡፡ እነርሱን እንደ ዳያስፖራ አንወስዳቸውም የተነጠሉ ናቸው፤›› በማለት የታሰበውን ያህል ገንዘብ መሰብሰብ ያልተቻለው ከተቃውሞ ጋር በተገናኘ እንዳልሆነ አብራርተዋል፡፡
የአገር ውስጥ አስተዋጽኦን በተመለከተ፣ ‹‹አሁን ካለበት መጨመር ነው እንጂ መልካም የሚባል ነው፡፡ ነገር ግን ከባለሀብቱ በኩል አንድ ዓይነትና ወጥ የሆነ አስተዋጽኦ አይደለም ያለው፡፡ ደከም ያሉ አሉ፣ ጥሩ የሄዱ አሉ፤›› ብለዋል፡፡
‹‹በድምር ውጤት ስንመለከተው ከውጤት አንፃር ከውጭና ከባለሀብቱ በቂ አላገኘንም ማለት ይቻላል፡፡ ከምንም በላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረከተው ሠራተኛው ነው፤›› ሲሉ አስታውቀዋል፡፡
የፕሮጀክቱን አፈጻጸም መንግሥት አሳንሶ እያቀረበ ነው የሚለውን አስተያየት በተመለከተ ምን ምላሽ እንዳላቸው ተጠይቀው በሰጡት ምላሽ፣ ‹‹የምናሳንስበት ምንም ምክንያት የለም፡፡ ደብቀው እየሠሩ ነው የሚሉ የተወሰኑ ጽሑፎች ተመልክቻለሁ፡፡ ነገር ግን ያለውን ነው እየገለጽን ያለነው፡፡ እንደዚያ ቢሆንልን እንመኝ ነበር፤›› ሲሉ አስተያየቱ መሠረተ ቢስ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡
በአሁን ወቅት ከአጠቃላይ የግድቡ ግንባታ 47 በመቶ የተጠናቀቀ መሆኑን፣ ለዚህም እስከ ሐምሌ 2007 ዓ.ም. በተሰበሰበ መረጃ መሠረት ከተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎችና ተቋማት ቃል ከተገባው ገንዘብ ውስጥ በአገር ውስጥ ሰባት ቢሊዮን ብር፣ በውጭ አገር ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ደግሞ 600 ሚሊዮን ብር መሰብሰቡ ተገልጿል፡፡
Reporter Amharic