የ44 ሚ. ብር ግብር ዕዳ ያለበት “ሪል ውሃ” ከፍተኛ ምርመራ እየተደረገበት ነው

የ44 ሚ. ብር ግብር ዕዳ ያለበት “ሪል ውሃ” ከፍተኛ ምርመራ እየተደረገበት ነው

    ቲ ጂ ኤም ዲ በሚል ስያሜ የተመሰረተው የ “ሪል ውሃ” አምራች ኩባንያ፤ ያለበት 44 ሚ.ብር የግብር ዕዳ በምርመራ ላይ መሆኑን የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ገለፀ፡፡ ኩባንያው ከ1999 ዓ.ም እስከ 2002 ዓ.ም ድረስ ታደለ ዳለቻ በተባለ ግለሰብ ስራ አስኪያጅነት ሲመራ የቆየ ሲሆን ከ2002 እስከ 2003 ዓ.ም አቶ ኤርሚያስ አመልጋ ይመሩት እንደነበር የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን የትምህርትና ኮሙዩኒኬሽን ምክትል ዳይሬክተር አቶ ፋሲካ በላይ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡ በመቀጠል ድርጅቱ አቶ መሃመድ ለተባሉ ግለሰብ የተሸጠ ሲሆን የኩባንያው እንቅስቃሴ ሲጠና ቆይቶ፣ 44 ሚ ብር የግብር እዳ እንዳለበት መታወቁን ይህንንም እዳ ግለሰቡ እንዲከፍሉ የሚጠይቅ ደብዳቤ በ2005 ዓ.ም ከባለስልጣኑ መ/ቤት እንደተፃፈላቸው ምክትል ዳይሬክተሩ አብራርተዋል፡፡ ግለሰቡ “ኩባንያውን ስገዛው ይሄ ሁሉ እዳ እንዳለበት አላውቅም’ የሚል ምክንያት አቅርበዋል” ያሉት አቶ ፋሲካ፤ አንድ ኩባንያ በሽያጭ ሲዘዋወር ክሊራንስ ሳይወጣበት ስለማይዘዋወር የሰውየው ምክንያት ተቀባይነት ያለው አልነበረም ብለዋል – አቶ ፋሲካ፡፡ በኋላ ግን ኩባንያውን የገዙት ግለሰብ ወደ ባለስልጣኑ በመቅረብ፤ “ያለበትን እዳ ቅድሚያ 25 በመቶ ከፍዬ ቀሪውን ቀስ በቀስ እከፍላለሁ” እያሉ ሲያዘናጉ ቢቆዩም፣ ኩባንያው ግን እስከ 2007 ዓ.ም ድረስ ማምረት አለማቆሙን ባለስልጣኑ ደርሶበታል ብለዋል ም/ዳይሬክተሩ፡፡ ኩባንያው ክስ ያልተመሰረተበት ጉዳዩ ውስብስብ በመሆኑ ነው ያሉት አቶ ፋሲካ፤ በአሁኑ ወቅት የግብሩ ዕዳ በከፍተኛ ምርመራ ላይ መሆኑን ኃላፊው ገልጸዋል፡፡የሪል ውሃ ማምረቻ ድርጅት ከ190 በላይ ሠራተኞች ያሉት ሲሆን ያለፉትን ሁለት ወራት ደመወዝ ያልተከፈላቸው መሆኑንና የሪል ውሃ ማምረቻው የሚገኝበት የቡራዩ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ፅ/ቤትም ለዓመታት ከሰራተኞቹ ደመወዝ የሚቆረጠው የስራ ግብር አልደረሰኝም ማለቱን ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ዘግቧል፡፡