የእናት አንጀት …. ዘመድኩን በቀለ


የእናት አንጀት ….
ዛሬ በማኅበራዊ ድረ ገጽ ላይ ያገኘሁት የእኚህ እናት ምስል ክፉኛ አስተክዞኛል ። እኝህ እናት ቢያንስ አዘቅዝቀው ያደረጉት ነጠላ እዚሁ ኢትዮጵያችን ውስጥ መሆናቸውን ይናገራል ። ለቀብር እየሄዱ መሆናቸውንም የያዙት አስከሬን ይናገራል ። ቦታው የት እንደሆነ ግን ፎቶውን ያነሳው ግለሰብም አልተናገረም ። አልገለጸልንም ።
እኚህ እናት ለቀብርስ እሺ ይሂዱ ። አስከሬኑን ያጠቡት ፣ ደግሞም የገነዙትስ እሳቸው ይሆኑ ? እሺ አስከሬን የሚሸከምላቸው ሰው እንዴት ጠፋ ? መቃብሩንስ ማን ቆፈረላቸው? ከቀበሩስ በኋላ በዚህ በያዙት ህፃን አስከሬን ላይ አፈሩን የሚመልሰው ማነው ? መቼም ይህ አስከሬን ከማህጸናቸው የወጣ ፍሬ ከሆነ በጣም ያሳዝናል ። እጅግ በጣም ያሳዝናል ። ተደራራቢና መቼም ከህሊና የማይጠፋ ሐዘን ነው።
እድር የሌለውን ሰው ፣ በአካል አይቶት የማያውቀውን እንግዳ እያለቀሰ ደረቱንም እየደቃ የሚቀብር ማኅበረሰብ ባለበት ሀገር ይህ እንዴት ሊከሰት ቻለ?
ከ90 ሚሊዮን በላይ ህዝብ ባላት ሀገር ላይ ምንድነው እንዲህ ያጨካከነን ። ይህን ምስል ያነሳው ሰው ፎቶ ከማንሳት ብትቀበላቸወ ምን አለበት? ብቻ ፎቶው ብዙ ነገር ይናገራል ።
ሰው የለም እንዳንል እግሩ ብቻ የሚታይ ትልቅ ሰው ፣ ከሩቅ የሚያዩ ሰዎች ፣ ቆሞ ፎቶ የሚያነሳ ሰው ይታያል ። የገጠር ከተማ በመሆኑም ብዙ ቤቶችም ይታያሉ ። እና የምን ጉድ ነው የምንስ መዓት መጣብን ? እንዴት ነው እስከዚህስ ድረስ እንዲህ ያጨካከነን ምን ይሆን ።
በእኔ በኩል በእኚህ እናት ላይ የደረሰ ሐዘን በማንም ላይ አይድረስ ። የፍቅር አምላክ ይታረቀን ።
ፎቶው ለምንም ይሁን በማን ዛሬ በፌስ ቡክ ላይ ተለጥፏል ። አነጋጋሪነቱም እንዲሁ ይቀጥላል ።
ዘመድኩን በቀለ ነኝ
ነሐሴ 5/12/2007 ዓም
አዲስ አበባ – ኢትዮጵያ