አደር ባዮች የዓላማ ፅናት ስለሌላቸው ፅኑዎችን ይረግማሉ፡፡ – ምንሊክ ሳልሳዊ
አደር ባዮች የዓላማ ፅናት ስለሌላቸው ፅኑዎችን ይረግማሉ፡፡ – ምንሊክ ሳልሳዊ –
ወያኔ ስልጣኑን ለማስረዘም ከሚጠቀምባቸው ስልቶች አንዱ በጥቅም የታሰሩ ሃሳብ የለሽ የሆኑ አደር ባዮችን መፈልፈል ነው። አድር ባይነት በየዘመን መለወጫው እንደልክፍት ብቅ ይላል፡፡ አብዛኞቹ አድር-ባዮች ሰብዕናን ባወጣው ዋጋ የሚሸጡ ናቸው፡፡ በዚህ ሽቀላና ደጅ-ጥናት ላይ የተሰማሩ ሁሉ፤ አቋም ለበስመ-አብ-ወልዱም ስለሌላቸው፤ አቋም ያለው አይጥማቸውም ወይም ከናካቴው ይጠላሉ፡፡ አደር ባዮች ቀን ለሰጠው መልካም መደላድል ለመሆኑ ዝግጁ ናቸው፡፡ ታዛቢ ዐይን ጠያቂ ታሪክ እንዳለ ይዘነጋሉ፡፡ የዓላማ ፅናት ስለሌላቸው ፅኑዎችን ይረግማሉ፡፡
መቼም በእኛ አገር፤ ዕውነተኛ ያልሆነው ነገር ዕውነተኛ ታሪክ ይበዛል ።ትውልድ ተስፋ እንዳይቆርጥ ተስፋ እናሳየው እንጅ በጥቅም እንዳይማልል ሰፊ ስራዎች መሰራት ያስፈልጋል፡፡ ለምርጫ ዕድል እንዳለው እናስተምረው፡፡ ወላዋይ ትውልድ እንዳንፈጥር እንጠንቀቅ፡፡በአምባገንኖች ስርአት ውስጥ አደርባይነት ማስፋፋት የገዢዎች ዋነኛ ተግባር መሆኑን እና በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ሆዳቸውን የሚሞሉ አደርባዮችን ሲሻቸው ልናስተምራቸው ካልጣማቸው ነቅሎ መጣል የትግሉ አንዱ አካል መሆኑን መዘንጋት የለብንም።
ወያኔ የመዋዠቅንና የአድር-ባይነትን ባህል በማስፋፋት ሁነኛ ህብረተሰብ በማክሰም ሆዳም ማህበረሰብ ለመፍጠር በመትጋት ላይ ስለሆነ ቀድመን መንቃት ያስፈልገናል፡፡ በተሳሳተ መንገድ የተሳሳተ አቅጣጫ ይዞ የሚሄድ ማህበረሰብ እንዳንይፈጠር ከልብ እንጣር፡፡ አድር-ባይነትን እና አደርባዮችን እናስወግድ፡፡ በትግሉ ውስጥ ፅናትና ዘላቂነት ከዕቅዳችን ጋር ይተሳሰሩ ዘንድ አለመዋዠቅ ሾውሸዌ አለመሆን ዋና ነገር ነው፡፡ ዕዳው በቀጥታ የራሳችን፤ በተዘዋዋሪ የልጆቻችን መሆኑን አለመዘንጋት ነው!