የአቶ ኤርሚያስ ለገሰ እና የዲያቆን ዳንኤል ክብረት የደብዳቤ ምልልስ – ለግንዛቤ እንዲያመች ደብዳቤዎቹን ያንበቡ
የአቶ ኤርሚያስ ለገሰ እና የዲያቆን ዳንኤል ክብረት የደብዳቤ ምልልሶች…ሶስቱም ደብዳቤዎች እዚህ ይገኛሉ
ከአቶ ኤርሚያስ ለገሰ ለዲያቆን ዳንኤል ክብረት የመጀመሪያ ደብዳቤ
ለዲያቆን ዳንኤል ክብረት ፣
ከአንድ ሰአት በላይ የፈጀውን ጥናታዊ ጵሁፍህን ሰማሁት። ሰምቼ ስጨርስ ደነገጥኩ። ከራሴም ጋር ለሰአታት ሙግት ገጠምኩ ። ኢህአዴግን ለቅቄ የወጣሁት ልቤ የፈቀደውን በነጳነት ለመናገር ነውና የማውቀውን እና የሚሰማኝን መናገር እንዳለብኝ ተሰማኝ ። ርግጥ በሐይማኖት ጉዳዬች ላይ መናገር ከባድ እንደሆነና ዋጋ እንደሚያስከፍል ጠንቅቄ አውቃለሁ ። በሌላ በኩል የሚያውቁትን አለመግለጵም የፀፀት ዋጋ አለው። በመሆኑም ባለመናገሬ ከሚሰማኝ ሙግት መናገሩን ስለመረጥኩ የሚከተለውን አጭር አስተያየት ለመስጠት ተገደድኩ።
1• ያቀረብከውን መረጃዎች እንዴት እንዳሰባሰብካቸው የተገለፀ ነገር የለም። በተለይም በድህረና ቅድመ ምርጫ 97 ባሉት ሶስት አመታት( ከኃላም ከፊትም) ያቀረብካቸውን መረጃዎች ምንጭ ማወቅ እፈልጋለሁ ። ይህን ጥያቄ የማነሳበት መሰረታዊ ምክንያቶች ስላሉኝ ነው።
1•1• በኢትዮጵያ አቆጣጠር 2001 አ• ም• ኢሕአዴግ ለሕዝቡ ይዞለት የመጣው እቅድ ” በአክራሪነት ” ስም ሀይማኖቶችን ማዳከም ነበር። ይህንንም ለማቀጣጠል እንዲረዳው በኢህአዴግ ቢሮ፣ በኮሙዩኒኬሽን ጵ/ ቤት፣ ፌደራል ጉዳዬች እና ፌደራል ፓሊስ መረጃ እንዲሰባሰቡ ተደረገ። የእስልምና ጉዳዬች ላይ ዝርዝር ጥናቱን እንዲሰራ የቤትስራ የተሰጠው ሽመልስ ከማል ነበር። ዛሬ አንተ ካቀረብክልን ውስጥ ግማሹ የቃላት ለውጥ እንኳን ሳይደረግለት በሽመልስ ከማል ጥናታዊ ፅሁፍ የቀረበ ነበር። በወቅቱ እጅግ ከመደንገጤ የተነሳ ሽመልስ እንዴት እንዲህ አይነት ጥናት እንደሰራ ለማወቅ ከጀርባው መጓዝ ነበረብኝ ። መጓዜ ያልጠበኩትን ውጤት አመጣ። ሽመልስ በእስልምና ላይ ከፍተኛ ጥላቻ የያዘው በቤተሰቡ ውስጥ በተፈጠረው ምስቅልቅል እድገት መሆኑን ተገነዘብኩ። አባቱ በአንድ ወቅት የመስኪድ አስተዳደር ነበሩ። በኃላ የሳውዲ ጉዞ አድርገው ሲመለሱ አስተዳደሩን በመነጠቃቸው ከሀይማኖቱ በተቃራኒ ተሰለፋ ። ” ከመካ መዲና ደርሶ መልስ” የሚል መጵሀፍ አሳትመው ክርስትና ተነሱ። ስማቸውም ወደ ሀይለየሱስ ተቀየረ። ባስታወቀው እርምጃ ቤታቸው ተመሰቃቀለ። ወንድማማች እና እህታማቾች የሚጠሩበት የአባት ስም እስከ መለያየት ደረሰ። ባጭሩ የሽመልስ ፀረ -እስላም የመሆን ምንጩ ይሄ ነው። በመሆኑም በሽመልስ ሲቀርቡ የነበሩ ዳታዎችና ትንታኔዎች እንደወረዱ ከአንተ ሲቀርቡ ስሰማ የመረጃ ምንጭህን ተጠራጠርኩ። በተለይ ቴኳንዶ ፣አክሱም፣ መያዶች …ወዘተ ብለህ የገለጵከው የካርቦን ግልባጭ ሆኖ አግኝቸዋለሁ።
1•2• ሌላኛው ዳታ የሰበሰበው የፌደራል ጉዳዬች ሚኒስተር የነበረው ዶክተር ሽፈራው ከፓሊስ ጋር በመሆን ነበር። ዶክተሩ ያጠናቀረው መረጃ ተመሳሳይ ሲሆን በማጠቃለያው ” የኦርቶዶክስ አክራሪነት አለ” የሚል ነበር። የአክራሪነቱ አስኳል ማህበረ ቅዱሳን እንደሆነ አፅንኦት ሰጥቶበት ነበር። ይህ የዶክተሩ መረጃ በአንተ ጥናታዊ ፅሁፍ ላይ አልቀረበም ።
( ግምቴን አስቀምጬ ለማለፍ ይህን የዶክተር ሽፈራው ዳታና ትንታኔ ለሌላ የእስልምና መምህር እንዲደርሰው ይደረግና እንደአንተ እንዲያቀርብ ይደረጋል ። ርዕሱንም ” የኦርቶዶክስ አክራሪነት ” ብሎ እንዲጠራው ይደረጋል ።)
2• የመረጃዎቹ ምንጭ እንደተጠበቀ ሆኖ ኩነቶቹ ሲፈጠሩ ሀገሪቷ የነበረችበትን ፓለቲካዊ ሁኔታ ከግምት አላስገባህም። ለምሳሌ ከምርጫ 97 በኃላ በኦሮሚያ የተከሰቱት የሐይማኖት ግጭቶች የተጠነሰሱት በአቶ መለስና ደህንነት ጵ/ ቤት ሲሆን ዋነኛ አሰፈጳሚዎቹ እነ አባዱላና የኦህዴድ ካድሬዎች ነበሩ። ” ቅንጅት የክርስቲያን ጠበቃ ነው” የሚለው መልእክት የተቀረፀው አንተ በጥናታዊ ጵሁፍህ ላይ ” ውሸት ሲደጋገም እውነት ይሆናል” የሚለው መርሆ አቀንቃኝ የሆነው አቶ በረከት ነው። በየጉራንጉሩ መልእክቱን ያሰራጩት ደግሞ ” እኔ ከሞትኩ… ” በሚለው ብሂል እነ አባዱላና ጁነዲን ናቸው። በተለይ በድሬደዋ የጠነሰሱት ሴራ ባይከሽፍ ኖሮ ዘግናኝ እልቂት ይከሰት ነበር። በመሆኑም ከምርጫ 97 በኃላ የተከሰቱት ግጭቶች ( በተለይ በኦሮሚያ) ጠንሳሾቹ አሁን እየመሩን ያሉት ፓለቲከኞች ሲሆኑ መንስኤውም ፓለቲካው የፈጠረው ነበር። አንተ ግን በየትኛው ቦታ ላይ የፓለቲከኞቹን ሚና ማንሳት አልፈለክም ። ይልቁንስ መንግስት አበረደው፣ መከላከያ አረገበው ማለትን መርጠሀል። ጥናትህን ሰፋ ብታደርገው ኢትየጵያ ውስጥ አክራሪነት በዋነኛነት እየሰፋ የሄደው በፓለቲካው መበላሸት ምክንያት የተፈጠረ መሆኑን ትደርስበት ነበር። አሁንማ በድጋሚ ለማየት ጊዜው አልረፈደም።
3• በጥናታዊ ጵሁፍህ ላይ በአሁን ሰአት ያለውን የኢትየጵያ ሙስሊሞች ” ኢትዬጲያዊነት የተላበሰ፣ ሰላማዊና ፍትሐዊ ጥያቄ” ማንሳት አልፈለክም ። እንደሚታወቀው የኢትዮጵያ ሙስሊሞች የተቃወሙት የመንግስት ጣልቃ ገብነት ነው።ኢህአዴግ ከሀይማኖቱ ላይ እጁን እንዲያነሳ ነው በሰላማዊ መንገድ እየጠየቁ ያሉት። አመራራችን በእኛ ይመረጡ፣ ተቋማችንን ራሳችን እናስተዳድር የሚል ነው። ለዚህ ደግሞ እኔ በየትኛውም ቦታና ሰአት ምስክር መሆን እችላለሁ። ታዲያ አክራሪን፣ አክራሪ ካልሆነው ለይቶ የማስረዳት አላማ ካነገብክ ለምን ፍትሐዊ የሆነውን ይህን ጥያቄ ሳታነሳ ቀረህ? እንደ ገዥዎቻችን ” የሙስሊሙ ጥያቄ አክራሪነት የወለደው ነው” የምትለን ከሆነም ወደ መድረክ አውጣውና እንነጋገርበት ።
4• አጀንዳህ ስለ ” ሙስሊም አክራሪነት ” ሆኖ ወደ ማጠቃለያህ ላይ በውጭ ሀገር ያለውን ሲኖዶስ ወደ መዝለፍ ለምን ተሸጋገርክ። ከአንደበትህ የወጣው ቃል ” የሐሰት ሲኖዶስ ተቋቁሞ መንጋ የማይጠብቅ ጳጳሳት ይሾማል ” የሚል ነው። ይህ ንግግር በራሱ አንድነት የሚያመጣ ነው? ውጭ ያለው ሲኖዶስ የሐሰት ነው / አይደለም ከሚለው ትርክት በፊት ይህ እንዲፈጠር ያደረገው ምክንያት ምንድነው የሚለውን ብታነሳ የተሻለ መልስ ታገኝ እንደነበር እገምታለሁ። ሐገር ቤት ያለውን ሲኖዶስ ማን ከጀርባ ሆኖ እንደሚያሽከረክረው ካላወክ በኢትዮጵያ ምህዳር ላይ መኖርህን እንድጠራጠር ያደርገኛል።
4• ሌላኛው ” ለምን አሁን?፣ ምን አዲስ ነገር አለ?” የሚል ጥያቄ እንዳነሳ አድርጐኛል ። የሙስሊሞች ሰላማዊ ትግል በተጠናከረበት፣ መንግስት በጅምላ ማሰር በጀመረበት ፣ ማህበረ ቅዱሳን ላይ በተዛተበት ወቅት ለምን የሚከፋፍል አጀንዳ ይዞ ብቅ ማለት ተፈለገ? የማን አጀንዳ ነው እየተራመደ ያለው የሚለውን ማየት ተገቢ ይሆናል ።
_______________________________________________________________________________________________________________________
ደብዳቤ ሁለት
ከዲያቆን ዳንኤል ክብረት ለአቶ ኤርሚያስ ለገሰ የተሰጠ ምላሽ
የኤርምያስ ለገሠን ‹ግልጽ ደብዳቤ› አነበብኩት፡፡ አንብቤው በሁለት ምክንያት ሳልጽፍለት ዘገየሁ፡፡ በአንድ በኩል ስለ ኤርምያስ ከነበረኝ የዋሕ ግምት የተነሣ ኤርምያስን ያህል ሰው ይህን ያህል አይሳሳትምና በቀጣዮቹ ቀናት በስሜ የወጣ ጽሑፍ ነው እንጂ የጻፍኩት እኔ አይደለሁም ይል ይሆናል ብዬ በመገመት፡፡ ጽሑፉ እንደወጣ ብዙ ሰዎች አሁን እኔ የምነግርህን ሲገልጡት ነበርና ትሰማቸዋለህ ብዬ አስቤ ነበር፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የሐዲስ ዓለማየሁ የባሕል ማዕከል ባዘጋጀው ዐውደ ጥናት ላይ ልካፈል ወደ ደብረ ማርቆስ ተጉዤ ስነበር፡፡
ከደብረ ማርቆስ ተመልሼ ገጸ ድሮቹን ሳሥሥ ግን ኤርምያስ ከነ ስህተቱ ጸንቶ አገኘሁት፡፡ ገሥግሦ የመጣን ደኅና አድርገህ ጫነው ነውና ለዚህ ሰው መንገር ያለብኝ ነገር አለ ብዬ አሰብኩ፡፡
ይህን ‹ግልጽ ደብዳቤ› ኤርምያስ አይጽፈውም ያልኩት እንዲህ ጊዜና ሁኔታን የማያገናዝብ ሰው ነው ብዬ ስላልገመትኩት ነው፡፡ አንድን ጽሑፍ ለመጻፍ ሲል ብቻ የሚጽፍ ሰው አድርጌ ስላልገመትኩትም ነው፡፡ ያንን መጽሐፉን በዕውቀትና በመረጃ ስለመሰለኝ ‹ቅዳሴው አልቆብህ ቀረርቶ ትሞላበታለህ› ብዬ ስላላመንኩ ነው፡፡
ኤርምያስ ሆይ፤
ይሄ አሁን አንተ አይተህ የደነገጥክለት ጽሑፍ አንተ ባዳመጥከው ጊዜ (በ2007 ዓም) የቀረበ ጥናት አይደለም፡፡ ምናልባት ‹ምንትስ የሰማ ለት ያብዳል› ሆኖብህ ካልሆነ በቀር፡፡ ጽሑፉ የቀረበው ነሐሴ 25 ቀን 1999 ዓም አሜሪካ፣ ዴንቨር ኮሎራዶ ከተማ ተደርጎ በነበረው ሰባተኛው የአሜሪካ ሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ጉባኤ ነው፡፡ የተለቀቀው ደግሞ ከአንድ ወይም ከሁለት ቀን በኋላ www.tewahedo.org በተሰኘ ገጸ ድር ነው፡፡
በዚያ ጥናት ውስጥ ‹አክራሪነት› የተፈረጀው ከእምነት አንጻር ነው፡፡ አክራሪ እስላም ስልም ‹‹በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ላይ ሆን ብሎ የጥፋት ዓላማ በመያዝ፣ የሕዝቡን አብሮ ተገናዝቦ የመኖር ሥርዓት በማፍረስ፣ አንዳንዴም የሌሎችን ዓላማ በማንገብና የቤት ሥራ በመውሰድ የተሠማራውንና እስልምናን ሽፋን የሚያደርገውን የጥፋት ኃይል ነው›››፡፡ ክርስቲያኖች ሁሉ ቅዱሳን ናቸው እንደማልለው ሁሉ ሙስሊሞች ሁሉ አክራሪዎች ናቸው ብዬ አላውቅም፡፡ አልልምም፡፡ ምክያቱም፣ ስላልሆነ፡፡
እስከ 2002 ዓ.ም ያለው ወቅት ማለት ደግሞ አንተ ራስህ በመጽሐፍህ እንደነካካኸው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ሕልውና ለማየት በማይፈልጉ ‹አክራሪ ሙስሊሞች› ቦታዋን የመንጠቅ፣ ካህናቷን የማረድ፣ ገዳማቷን የማቃጠል፣ ቅዱሳት መጻሕፍቷን የመዝረፍና ወደ ባዕድ ሀገር የማሻገር እኩይ ተግባር ይከናወን የነበረበት፣ እንዲያውም ሁኔታው ራሱ ጫፍ የደረሰበት ጊዜ ነበር፡፡
አንተ ዛሬ ስትወጣ በሌሎች ብቻ አመካኘኸው እንጂ በአዲስ አበባ አየር ጤና ኪዳነ ምሕረት የጥምቀት ቦታ ክርክር ጊዜ የመንግሥትን ሥልጣን ይጠቀሙ ከነበሩት ሰዎች አንዱ ነበርክ፡፡ በወቅቱ እኔ የማኅበረ ቅዱሳን ሚዲያዎች ኃላፊ ነበርኩ፡፡ ጉዳዩን ከእግር እስከ ራሱ ዐውቀው፣ እከታተለውም ነበር፡፡ መረጃዎቹንም ከየአቅጣጫው እናገኝ ነበር፡፡ አጠናቅረንም በጋዜጣ እናወጣ ነበር፡፡ በዚያም ምክንያት አያሌ ጫናዎችን ካደረሱብን ሰዎች አንዱ አንተ ነበርክ፡፡ ቢሮህ አስጠርተህን ቤተ ክርስቲያኒቱንና የፈረደበትን አማራ ምን ብለህ እንደተሳደብክ የምናውቀው አንተ እና እኛ ነን፡፡
ከአሰቦት መነኮሳት የ1984 ዓም መታረድ በኋላ በሚዲያ ዋና ክፍል እኔና ጓደኞቼ ከሠራናቸው ሥራዎች መካከል አንዱ አክራሪ ሙስሊሞች በቤተ ክርስቲያኒቱ ከጥንት እስከ ዛሬ ያደረሱትን፣ ሊያደርሱትም ያሰቡትን መረጃ ማሰባሰብ ነው፡፡ አንዳንዶቹን በቦታው ተገኝተን፣ ሌሎቹን ከቦታው በሚመጡ መረጃዎች፣ የቀሩትንም ከተለያዩ የመረጃ ምጮች አሰባስበናቸው ነበር፡፡ ከሚመለከታቸው የውጭ ዩኒቨርሲቲዎችና የመረጃ ምንጮችም በውድ ዋጋ የገዛናቸው ነበሩ፡፡
በነገራችን ላይ ያ ጽሑፍ በፕሮጀክተር ታግዞ ቀርቦ ስለነበር የመረጃ ምንጮቹን የሚያሳየው የጎንዮሽ ማስተዋሻን ማንበብ አላስፈለገም፡፡ ለዚህ ነው ምንጩን የድምጹ መልእክት ላይ ያላገኘኸው፡፡ የድምጹን መልእክት የለቀቅኩትም እኔ አልነበርኩም፡፡ የኦርቶዶክስን ትምህርቶች በመረጃ መረብ በመልቀቅ የሚታወቀው www.tewahedo.org የተሰኘ ገጸ ድር ነው፡፡ ዛሬም በዚሁ ገጸ ድር ላይ ስላለ ማየት ትችላለህ፡፡ ወይም አዘጋጁን በገጸ ድሩ ላይ ባሠፈረው የመመየሊያ አድራሻው(email)ብትጠይቀው የሚነግርህ ይመስለኛል፡፡
አንተን ወደ ባሰው ስሕተት የወሰደህ የተሟላ መረጃ ሳታገኝና ለማግኘትም ሳትፈልግ ወደ ድምዳሜ መንደርደርህ ነው፡፡ የመጀመሪያው፣ እኔ ጥናቱን በ1999 ዓም ዴንቨር ኮሎራዶ፣ በ2000 ዓም አዲስ አበባ ደብረ ገሊላ ዐማኑኤል ቤተ ክርስቲያንና በዮርዳኖስ ሆቴል (ማኅበሩ ስለ ሚሊኒየም ባዘጋጀው ጉባኤ) ካቀረብኩት በኋላ ነው ‹ሽመልስ ከማል ሠራው› ያልከው ጥናት ለመንግሥት የቀረበው፡፡ ያ ጥናት ለመንግሥት አካላት ሳይለዋወጥ መቅረቡን በወፍ በረር እናውቅ ነበር፡፡ ስለዚህም የተከተለ ከቀደመ ይወስዳል እንጂ የቀደመ ከተከተለ አይወስድምና ‹ቃላት ሳይቀየሩ የቀረበው› እኔ ያቀረብኩት ጽሑፍ እንጂ በእናንተ ስብሰባ ላይ የቀረበው ጽሑፍ ወደ እኔ መጥቶ ሊሆን አይችልም፡፡ አንተ ራስህ በመጽሐፍህ ውስጥ አድንቀህ የጠቀስከው የአቡነ ሳሙኤል መጽሐፍኮ ይህንን ዋቤ አድርጎ የተጻፈ ነበር፡፡ እርሳቸውም ‹ከሽመልስ ከማል ወስደው› ነው ልትል ነው?
ሁለተኛው ስሕተትህ ቤተ ክርስቲያኒቱንና የቤተ ክርስቲያኒቱን ልጆች የምታይበት ዓይንህ ዛሬም አለመስተካከሉን የሚያሳየው ስሕተት ነው፡፡ ይህቺ ቤተ ክርስቲያን የሚቆረቆሩ ብቻ ሳይሆኑ መሥዋዕት ሆነውም ታሪክ የሚሠሩ ልጆች አሏት፡፡ እነዚያ ልጆች ናቸው አይገቡ ገብተው እነዚያን መረጃዎች የሰበሰቧቸው፡፡ አንዳንዶቹን መረጃዎች ለማግኘት እንደ ሠለስቱ ደቂቅ በእሳት ውስጥ ማለፍን ይጠይቅ ነበር፡፡ አንተና ሌሎቻችሁም የደነገጣችሁት ‹‹ሰው በቅንዐተ እምነት ተነሣስቶ እንዲህ አይሠራም፣ ሌላ ከጀርባው አንድ ነገር አለ›› ብላችሁ ስለምታምኑ ነው፡፡
በበሻሻ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያን ጅማ ውስጥ በጥቅምት 1998 ዓም አክራሪ ሙስሊሞች በየዋሐን ምእመናንና ካህናት ላይ የፈጸሙትን ግድያ ሕዝቡ ሲሰማኮ አንተና ሌሎቻችሁም ጣታችሁን እኛ ላይ ጠቁማችሁ ስንት ቀን እሥር ቤት አመላልሳችሁናል፡፡ አንተ ራስህ በመጽሐፍህ የገለጥከው ራስህ ቆመህ ያስፈረስከውን ቤተ ክርስቲያን በተመለከተ በድፍረት መጀመሪያ የዘገብነው በስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ላይ ነበር፡፡ ያኔ ምን እንዳላችሁን ታውቃለህ፡፡
ሦስተኛው ስሕተትህ ‹የዶክተር ሺፈራው ጥናት ለምን በአንተ ጥናት ውስጥ አልቀረበም?› የሚለው ነው፡፡ ለምን ይቀርባል? እኔኮ የራሴን ጥናት ሠርቼ በራሴ መድረክ ላይ ነው ያቀረብኩት፡፡ 1999 ዓም ከ2001 ዓም በኋላ የሚመጣ ነው ካላልከኝ በስተቀር፤ በኋላ የተደረገ ጥናት እንዴት ተደርጎ ነው በፊት በተሠራ ጥናት ውስጥ የሚካተተው?
የዛሬ 8 ዓመት ጥናቱ ሲሠራ ያገኘናቸውንና ያመንባቸውን መረጃዎች ተጠቅመናል፡፡ ያ ማለት ግን ሁሉን ዐውቀን ነበር ማለት አይደለም፡፡ አንተ ጉዳዩን ሲያባብሱ ነበሩ ያልካቸው ባለ ሥልጣናት አክራሪነትን ሲመሩትና ሲያቀጣጥሉት ነበር ካልክ መረጃውን በበቂ ሁኔታ አንተ በቦታው የነበርከው ንገረን፡፡ ከዚያ ውጭ መከላከያ ሠራዊት ያደረገውን ጥረት ግን በአካል በመገኘት ጭምር ዐውቀዋለሁና ልዋሽ አልችልም፡፡ የተወሰኑ የመንግሥት አካላት የወሰዱትን በጎ ርምጃም ልዋሸው አልችልም፡፡ እውነት ነበርና፡፡
እጅግ ያስገረመኝ ደግሞ ‹በጥናታዊ ጽሑፍህ አሁን ያለውን የሙስሊሞች ሰላማዊ እንቅስቃሴ ለምን አላነሣህም?› ብለህ የጠየቅከው ጥያቄ ነው፡፡ ለመሆኑ ይኼ እንቅስቃሴ ጥናቱ በቀረበበት በ1999 ዓም ተነሥቶ ነበር? ወይስ ለምን ወደፊት ይመጣል ብለህ ትንቢት ለምን አልተናገርክም ማለትህ ነው? ስሜ ነው እንጂ እኔኮ ነቢይ አይደለሁም፡፡ እንዲያ ከሆነ ደግሞ አንተም ስምህ የነቢይ ነውና በኋላ በኢሕአዴግ ውስጥ ደረሰ የምትለውን ችግር ቀድመህ ዐውቀህ ለምን ከአባልነት አልታቀብክም? የሚል ጥያቄውን ስትመልስ እመልስልሃለሁ፡፡
ስለ ‹ስደተኛው ሲኖዶስ› አቋሜን በተደጋጋሚ ገልጫለሁ፡፡ የፖለቲካውን ገጽታ አንተ ንገረን፡፡ በክርስትናው ግን መንጋውን ጥሎ የሚሄድን እረኛ ጻድቅ የሚያሰኝ ነገር ስላላገኘሁ ነው፡፡ ‹የቅዱስ ሲኖዶስ መንበሩ አዲስ አበባ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ነው› የሚለው የቅዱስ ሲኖዶስ ደንብ የወጣውኮ አሁን በስደት ያሉት አንጋፋዎቹ አባቶች አዲስ አበባ እያሉ በ1972 ዓም ነው፡፡ ያንን የማክበር ግዴታ የሁሉም ነው፡፡ ‹አባት አንጂ መንበር አይሰደድም› የሚለው ደግሞ ዛሬም ነገም አቋሜ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ተቃዋሚዎች እንኳን ተሰድደው ፓርቲ አቋቋሙ እንጂ መንግሥት አላቋቋሙም፡፡ በምን ቀኖናዊ መብት ነው ተሰድዶ መንበር ማቋቋም የሚቻለው? ከመንበሩ ውጭ ሆኖ ሀገረ ስብከቱን ያስተዳደረ አንድ ሲኖዶስ እስኪ በታሪክ ይጠቀስልኝ? እኔ አንተን ጥቀስ ብዬ አላስቸግርህም፡፡
‹መንግሥት በቅዱስ ሲኖዶስ ጫና ማድረጉና ጣልቃ መግባቱ› ተቀባይነት የሌለውና የምእመናንን ገድል የሚጠይቅ መሆኑ ባይካድም አሁን ያሉትን አበው ብቻ የሚመለከት ወቀሳ ግን አይደለም፡፡ ለቤተ ክርስቲያናችን አንዱ የዘመኑ ተግዳሮት ብሔራዊ ሲኖዶስ ከተቋቋመ ጀምሮ ከመንግሥት ተጽዕኖ ነጻ የሆነ ሲኖዶስ አለመኖሩ ነው፡፡ ያ ማለት ግን ለእምነታቸው የሚሞቱ፣ ለእውነት የሚሟገቱ አበው በቅዱስ ሲኖዶስ ውስጥ የሉም ማለት አይደለም፡፡ አንተ ራስህ ይህንን በመጽሐፍህ ስለጠቀስከው ለቀባሪ አላረዳም፡፡
እዚህ ላይ ግን በግልጽ ልነግርህ የምችለው የመንግሥት ባለ ሥልጣናት በተወሰኑ አባቶች ላይ ተጽዕኖ ሊያደርሱ ይችሉ ይሆናል እንጂ አንተ እንዳልከው ቅዱስ ሲኖዶሱን እስከ ማሽርከር የሚደርስ ዐቅም ፈጽሞ የላቸውም፡፡ቢኖራቸው ኖሮ አንተ ራስህ ተገኝተህ የታዘብከውን የአባቶች ጥንካሬ ማየት አትችልም ነበር፡፡ በ2006 ዓም በሰበካ አጠቃላይ መንፈሳዊ ጉባኤ የተገኙትን የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ተወካዮች በመረጃና ማስረጃ ሲወጥሩ፣ እምነታቸውን ሲመሰክሩና ያለ ፍርሃት ሲናገሩ እኔ ራሴ አባቶቼን በዓይኔ አይቻቸዋለሁ፡፡ ይህን ያደረጉት አሜሪካ ሆነው አይደለም፡፡ በቢላዋው ሥር ሆነው እንጂ፡፡
‹ለምን አሁን ቀረበ?› ብለህ የጠየቅከኝ በ2000 ዓም ቢሆን ኖሮ አብራራልህ ነበር፡፡ ጥናቱ የቀረበው በ1999 ዓም፣ አንተ ጥያቄውን ያነሣኸው ደግሞ በ2007 በመሆኑ ‹ይለፈኝ› እልሃለሁ እንደ ጋይንት ሰው፡፡
በመጨረሻ ኤርምያስ ሆይ
‹ብለነው ብለነው የተውነው ነገር
ባሏ ትናንት ሰምቶ ታንቆ ሊሞት ነበር›
የተባለው ደርሶብህ፤ ማጣሪያና ማብራሪያ ሳታገኝ ወርደህ በመጻፍህ፤ ገረመኝም አሳዘነኝም፡፡ የገረመኝ ‹አንተን የሚያህል› ብዬ የማስብህ ሰው ሁለቴ እንኳን ሳይለካ ለመቁረጥ በመቸኮሉ፤ ያሳዘነኝ ደግሞ ‹ኤርምያስ ሌላውንም ነገር የሚነግረን እንዲህ አመክንዮአዊ ሐሰት ይዞ ነው ማለት ነው› እንድል ስላደረገኝ ነው፡፡ አመክንዮአዊ ሐሰት ማለት በአቀራረቡ ተጠየቃዊ የሆነ፣ ነገር ግን በስሕተት መረጃዎች የተሞላ ማለት ነው፡፡
በመጨረሻ ዳዊት ለሳዖል የዘመረውን መዝሙር ልጋብዝህ
‹ኃያላን እንዴት ወደቁ›
_______________________________________________________________________________________________________________________
ለዲያቆን ዳንኤል ክብረት ( የመጨረሻ አስተያየት)
በመጀመሪያ ጊዜህን ሰጥተህ የጠየኩትን መረጃ ስለሰጠኸኝ ምሥጋናዬ ይድረስህ። በተደጋጋሚ እንደገጵኩት የአንተን የድምጵ መልእክት የሰማሁት ማስታወሻውን ከመጳፌ በፊት በማህበራዊ ድረገጶች በሰፊው እየተራገበ በመመልከቴ ነው። አንተ እኔን ለመወረፍ እንደሞከርከው ” ጊዜና ሁኔታ ያላገናዘበ” ሳይሆን አጀንዳውን ጐትተው ወደ መድረክ ያመጡት ወቅታዊ በመሆኑ ነው። ( በፌስ ቡክ ላይ የተለቀቀበትን ቀን መመልከት ትችላለህ)
ከአንዳንድ ወዳጆቼ ጋር በነበረን ምልልስ እንደገለፅኩት ይህን ሰነድ ወደ ፊት ይዞ መምጣት አሁን የሚደረገውን የኢትየጵያ ሙስሊሞች የነፃነት ትግል ጥላሸት ለመቀባትና ለመቀልበስ በማሰብ ነው። ባጭሩ ያቀረብከው ሰነድ መቼም ይሁን መቼ ” ጊዜውን እየጠበቀ የሚፈነዳ ፈንጂ” መሆኑን አስምሬበታለሁ። አሁንም እምነቴ ይህ ነው።
በዝርዝር ካነሳሀቸው ጉዳዬች አንዳንዶቹን ነቅሼ በማውጣት ነጥብ በነጥብ አስተያየት ልስጥበት፣
1• ” ኦርቶዶክስና የአማራ ፓለቲካ”
እጅግ በጣም የገረመኝ ከኪዳነ ምህረት ቤተክርስቲያን ጋር ተያይዞ ” ቢሮህ ጠርተኸን የፈረደበትን አማራ” ሰደብክ ብለሃል። በጣም አዝናለሁ። ሰዎች ፊት ቆመህ የምትሰብከው እንደዚህ አይነት የከረፋ አመለካከትና ውሸት ተሸክመህ መሆኑን መመልከቴ ርግጥም አሳዝኖኛል ።
ሲጀመር ከኪዳነምህረት ቤተክርስቲያን ጋር በተያያዘ አንተንም ሆነ ሌሎች የኦርቶዶክስ ሐይማኖት አባቶችን ቢሮ ጠርቼ አላናገርኩም። በመጵሀፌ ላይ እንደገለፅኩት መስኪዱ እንደሚገነባ የሰማሁት በምሳ ሰአት፣ የተገነባው የዛኑ ቀን ለሊት ነበር። ወደ ቢሮዬ የተመለስኩት ደግሞ መስኪዱ ተገንብቶ ባለቀ በሶስተኛው ቀን ። ርግጥ በወረዳ 23፣24 ፓሊስ ጣቢያ የዞኑ ፓሊስ አዛዥ ( ኮማንደር ተሰማ) እና የወረዳው ፓሊስ አዛዥ ( ኮማንደር ተስፋ ፈርሻ) ጋር በመሆን በቁጥጥር ስር ውለው ከነበሩ አባቶች ጋር ተወያይተናል ። ታዲያ ከአንተ ጋር ቁጭ ብዬ ባልተነጋገርኩበት እንዲህ አይነት ቅጥፈት ከየት አመጣኸው?
( በዞን ሁለት በነበረኝ ቆይታ ከአዲሳአባ ሀገረ ስብከትም ሆነ ሲኖዶሱ ጋር የተወያየሁት በቅድስት ልደታ ቤተክርስቲያን እና በጐፋ ገብርኤል በተነሳው ችግር ምክንያት ብቻ ነው። እሱም ቢሆን እኔ፣ ደረጄ ( የወረዳ 22 አስተዳዳሪ) ፣ መኮንን ( ፓሊስ አዛዥ) እና ፊዬሪ ( የሚሊሻ ጵ/ ቤት ሐላፊ) ወደ ተጠቀሱት ቦታዎች ሄደን እንጂ እነሱ መጥተው አይደለም ። በወቅቱ ከጳጳሱ ( ነብሳቸውን ይማረውና) የደረሰብን ማስፈራሪያ እና በእሳቸው ዛቻ ምክንያት የተፈጠረው ቀውስ የቤተክርስቲያኗን ክብር ስለሚነካ ከመግለፅ ተቆጥቢያለሁ። አንዳንድ ወዳጆቼ ለምን አስቀረኸው የሚል ወቀሳ ቢቀርብብኝ ህውሀትን ለማጋለጥ ሃይማኖቱን አላዋርድም በሚለው ጵናቴ ትቼዋለሁ።)
” የፈረደበት አማራ” የሚለው ቅፅል የጵሁፍህ አንዱ ማጠንጠኛ እንደሆነ ለመገንዘብ በህውሀት ፓለቲካ ውስጥ አንድ ወር መቆየት በቂ ነው። ኦርቶዶክስና አማራን ህውሀት ጠላት አድርጐ እንደዘመተባቸው ስለምታውቅ እኔን በ” ፀረ አማራ” ፈርጀህ ብትጵፍ ሚዛን እንደሚደፋልህ የተቀመረች ” አቦይ ስብሀታዊ” ሂሳብ ሰርተህ መጣህ። ሐይል ለማሰባሰብ ተጠቀምክበት። አዲሳአባ ከኦሮሞና አማራ ተወልዶ፣ አድጐ፣ አማራ አግብቶ ለሚኖር ሰው ” ፀረ – አማራ” ታፔላ ለመለጠፍ ህሊናህ እና እምነትህ እንዴት እንዳልገቱህ ሳስበው እጅጉን ገርሞኛል ። ርግጥ ዘርን ጐትቶ ወደ እምነት ተቋማት ማምጣት( በተለይ ኦርቶዶክስና አማራ) የማን የፓለቲካ ቁማር እንደሆነ አንተም፣ እኔም፣ አንባቢያንም፣ ” ኢትዬጲያም” …ወዘተ እናውቀዋለን ። በዚህ ምክንያት ” አቦይ የላከው…” እንድልህም አስገደደኝ። በአንድ ወቅት ስብሐት ነጋ በሚመራው ” የሰላምና አለም አቀፍ ምናምንቴ ኢንስቲትዩት ” ኔትወርክ እንድትታቀፍ ካድሬዎች ሊመለምሉህ እንደሆነ ስለማውቅ ። መጨረሻውን ባላውቀውም።
2• ” መወደሰ መከላከያ ሰራዊት ”
ህውሀት የተፈጠረውንና የጭቆና መሣሪያ ሆኖ የሚያገለግለው መከላከያ እውቅና የሰጠህበት ምክንያት አሁን ላይ ስመለከተው በጣም ግልፅ ሆኖልኛል ። ህውሀት የእምነት ተቋማትን በተጠና እና በታቀደ መልኩ ይበጠብጣል። ከዛም እርስ በራስ ያጨፋጭፋል። በመጨረሻም መከላከያ ( የፀጥታ ሀይል) ገብቶ አበረደው የሚል ፕሮፐጋንዳ ይረጫል ። በተለይ ከምርጫ 97 በኃላ የተፈፀሙ ድርጊቶች ቅኝት ይሄ ነበር። ስለዚህ ግልፅ የሆነልኝ ነገር ከጀርባ ምን እንደሚሸረብ አታውቅም አሊያም ለመካድ ፈልገሀል። አሊያም እንደገለጵከው ፓለቲከኛ አይደለህም ።
3• ጥናቱ ለመንግሥት ስለመቅረቡ
በምላሽህ ላይ ” ያ ጥናት ለመንግስት አካላት ሳይለዋወጥ መቅረቡን በወፍ በረር እናውቅ ነበር።” አየህ! ዲያቆን ዳንኤል ትልቁ ነጥብ ይህ ነው። በጥናቱ ውስጥ ያሉትን መረጃዎች እንደወረደ ለመጀመሪያ ጊዜ የሰማሁት በ2001 አ•ም• ከሽመልስ ከማል ነበር። ይህንን ጥናት መሰረት በማድረክ የመወያያ ሰነድና የድርጊት መርሐ ግብር ተዘጋጀ። ( ዶክመንቱን በአዲስ ራዕይ መፅሔት ላይ ይገኛል)
በተዘጋጀው ሰነድ ( ከግማሽ በላይ የአንተ ዶክመንት አባሪ የተደረገበት)ከአራት ሚሊዬን በላይ በሆኑ የኢህአዴግ አባላት ውይይት ተደረገበት። በጣም የሚገርመው አብዛኛው አባል በተለይ ኦሮሚያ እና አማራ ክልል ተቃውሞ ገጠመው። ሆን ተብሎ ክርስቲያንና ሙስሊሙን ለማጋጨት የታቀደ ነው የሚል ግዙፍ አስተያየቶች ተስተናገዱ። በተለይም “አክራሪነት በክርስትናም ፣ በእስልምናም አለ!” የሚለው ድምዳሜ ብዙዎችን አስቆጣ። የእኛ አባላት የሆኑ የዩንቨርስቲ ተማሪዎች በእኛ ተቃራኒ ተሰለፋ። እውነቱ ይሄ ነው። የሕውሐት ፓለቲለካ በማወቅም ሆነ ባለማወቅ አንተ አዘጋጀሁት ያልከው ሰነድ ይህን ሁኔታ ፈጥሯል። በዚህ ጉዳይ ለተፈጠረው ችግር ድርሻህን እንደመውሰድ ዛሬም በማር የተለወሰ አባባል ይዘህ ብቅ አልክ።
እስቲ ከጳፍከው ውስጥ የሚከተለው አርፍተነገር ምን ለማለት አስበህ እንደሆነ አስረዳኝ?
” ክርስቲያኖች ሁሉ ቅዱሳን ናቸው እንደማልለው ሁሉ ሙስሊሞች ሁሉ አክራሪዎች ናቸው ብዬ አላውቅም ”
ይህን አርፍተነገር እንገልብጠውና ፣ የተገለበጠውን የምታምንበት ከሆነ አክብሮቴን ከወዲሁ እገልጳለሁ። እስቲ ልገልብጠው ( እድሜ ለማቲማቲክስ!!)
” ሙስሊሞች ሁሉ ቅዱሳን ናቸው እንደማልለው ሁሉ ክርስቲያኖች ሁሉ አክራሪዎች ናቸው ብዬ አላውቅም”
ቀጣዩ ተግባር በድርጊት መርሐ ግብሩ መሰረት ወደ ተግባር መግባት ነበር። ለኢትየጵያ እስልምና ተከታዬች አዲስ ዶክትሪን በመንግስት መሪነት ተዘጋጀ፣ ከቀበሌ እስከ መጅሊስ የሚሆኑ አመራሮች በኢህአዴግ ተመረጡ ( በዚህ እንቅስቃሴ ውስጥ ተዋንያን ነበርኩ። ለዚህም ነው አንዳችም የሕውሐት ሸፍጥ መደበቅ የለበትም ብዬ በድፍረት የምናገረው።) እናም ጐበዝ ከሆንክ በኢትየጵያ ሙስሊሞች ላይ ህውሀት የሚያደርሰውን ጭቆና በአደባባይ አውግዝ!!
ኦርቶዶክስ ጋርም ጫናው ተመሳሳይ ነው። አባይ ፀሐዬ የተናገራት በሙሉ ተፈፅሟል ። በጣም የሚያሳዝነው የአባይ ፀሐዬን የድብብቆሽ ጨዋታ ልቦናህ እያወቀ ” የሲኖዶሱን የፓለቲካ ገጵታ አንተ ንገረኝ ” ትለኛለህ። ” ንገሩኝ ባይ! ” እንዳልልህ ላጠለከው ቆብ ክብር መንሳት ሆኖ ተሰማኝ። ሲኖዶሱ ህውሀት እንዴት እንደሚያሽከረክረው ለማወቅ እንዲሁ በመንገድ ላይ የሚሄድ ወጣት አቁምና ጠይቅ። አንተ የፈራኸውን የፓለቲካ ቁማር ይነግርሀል። ተመራምረህ ጥናታዊ ፅሁፍ ማዘጋጀት ከፈለክ ደግሞ ” ብታምኑም ባታምንኑም ሲኖዶሱ በቀኝ ግዛት ተይዟል ” ያሉትን አባት እንደመነሻ ለመጠቀም ፍቃድህ ይሁን።
