የሰማያዊ ፓርቲ አባል ከዕጩነት እንዲወጣ የምርጫ አስፈጻሚው አማላጅ እንደላከበት ገለጸ (ነገረ ኢትዮጵያ)
በደጋ ዳሞት ወረዳ ሰማያዊን ወክሎ በዕጩነት የቀረበው አቶ ግርማ ቢተው በተመዘገበበት የምርጫ ወረዳ በምርጫ አስፈጻሚነት እንዲሰራ የተመደበው አዱኛ አለማየሁ የተባለ ግሰለሰብ ከዕጩነት እንዲወጣ አማላጅ እንደላከበት ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጾአል፡፡
‹‹በምርጫ አስፈጻሚነት የሚሰራው ሰው 97 ላይ የፖሊስ ጣቢያ አዛዥ ነበር፡፡ ከቅጽ 3 ወደ ቅጽ 4 ለመዘዋወር እፈልግሃለሁ ካለኝ በኋላ ሲያመላልሰኝ ሰነበተ፡፡ አማላጅ ከላከብኝ በኋላ ከዕጩነት እንደማልወጣ በመግለጼ ታስሬያለሁ፡፡ ከእኔ ጋር ተገናኝተዋል የተባሉ ሰዎችም ታስረዋል፡፡››
ሲል አቶ ግርማ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጾአል፡፡
አቶ ግርማን ለማግባባት በአማላጅነት የተላኩ ሁለት ኢንስፔክተሮች ‹‹ይቅርብህ፡፡ ከቸገረህ ከኢህአዴግ ጋር ብትሰራ ይሻላል፡፡›› ብለው ለማግባባት ሲሞክሩ ባለመቀበሉ ከዕጩነት ካልወጣ እርምጃ እንደሚወስዱበት እንዳስፈራሩት ገልጾአል፡፡ ‹‹በማባበያውም ሆነ በማስፈራሪያው ከዕጩነቴ ልውጣ ፈቃደኛ ባለመሆኔ የአንድነት አባል የሰማያዊ ፓርቲ ዕጩ እንዳይቀርብ ተቃውሞሃል፡፡›› በሚል ሳይመዘግቡት እንደቀሩ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጾአል፡፡
የዚህን አመት “ምርጫ” ልዩ የሚያደርገው አገዛዙ ተመራጭ ሆኖ መቅረቡ ሳይሆን የእጩ ተወዳዳሪ ፓርቲዎችንና እጩ ተወዳዳሪዎችን መራጭ መሆኑ ነው። የአንድነት ፓርቲ በምርጫ ቦርድ ታግዶ የድርጅቱ እውቅና ከዚህ በዚት በተደረጉ ምርጫዊች አንድ ድምጽ ብቻ (እርሱም የራሳቸውን) ድምጽ ላገኘው የትግስቱ ቡድን መስጠቱ ይታወቃል። ምርጫ ቦርድ እውቅናዉን ለአንድነት ሲሰጥ ፣ ፓርቲው ሕልዉናው እንዲቀጥል የሚል ምክንያት ነበር የሰጠው። ሆኖም የትግስቱ ቡድን የፓርቲውን ሥራ ሲሰራ አልታየልም። በአቶ በላይ ፍቃዱ የሚመራው አንድነት ከ480 በላይ ተወዳዳሪዎች ለፓርላማ፣ ከ900 በላይ ተወዳዳሪውች ለክልል አዘጋጅቶ እንደነበረ ይታወቃል። ፓርቲው በሳምንት ሁለት ጋዜጦችን በማተም አማራጭ ፖሊሲዎች ወደ ሕዝብ በማድረስ፣ ከፍተኛ የሆነ ሰላማዊና ሕዝባዊ እንቅቃሴዎች በትጋት እየሰራ ነበር።
ሆኖም ይይህ አይነቱን ዉጤት የሚያመጣ አመራር ማቆም ያስፈልጋል የሚል የፖለቲካ ዉሳኔ ተወስነ። ለተለጣፊው ቡድን ድርጅቱ በኃይል ተሰጠ። ድርጅቱን እነ ትግስቱ ከተረጀቡ በኋላ የፓርቲው ሥራ ቆሟል። ጋዜጦችን አልታተሙም። በየከፍለ ሃገራቱ ያሉ የአንድነት መዋቅሮች ጠቅለለው ሰማያዊ ፓርቲን በመቀላቀላቸው ፣ ሕወሃት የአንድነት አባላትን አቶ ትግስቱን ካልተቀላቀላችሁ በሚል ወከባ እየደረሰባቸው ነው።
ከአንድነት ቀጥሎ ፣ በርካታ የአንድነት አባላት ስለተቀላቀሉት ሰማያዊ ጠንካራ ተፎካካሪ ሆኖ ቢቀርብም፣ አንድነት ላይ እንዳደረጉት የሰማያዊ ፓርቲን ለጊዜው ባያግዱም፣ ሕወሃቶች የሰማያዊ ተወዳዳሪዎችን መሰረዝ ጀምረዋል። ሊቀመነበሩ ሳይቀር ለምርጫ እንዳይወዳደሩ ተደርጓል። የአገዛዙ ዱላ በጠነከረ መልኩ ሰማያዊ ላይ እያረፈ ይገኛል።
በዚህ ሁኔታ በምርጫው መቀጠሉ ምን እርባና ሊኖረው እንደሚችል ግልጽ ባይሆንም፣ የሰማያዊ አመራሮች በ15 ከተሞች ሕዝባዊ እንቅስቃሴ ለማድረግ ዝግጅት ላይ እንዳሉ ይናገራሉ።
በምርጫዉ ዙሪያ የዚህ ሳምንት ዳሰሳን ለማንበብ እታች ይመልከቱ
ሳምንቱና ምርጫ ( ከየካቲት 9-15)(mircha.org)
ከሳምንት ሳምንት አግራሞት የማያጣው የሚቀጥለው ምርጫ በዚህ ሳምንት የእጩዎች ስረዛ ትልቅ የመነጋገሪያ ርእስ ሆኗል፡፡ ፓርቲዎች እጩዎች ምዝገባን አስመልክቶ የደረሱባቸውን ተግዳሮቶች በተደጋጋሚ ሲገልጹ የከረሙ ሲሆን የተለያዬ መግለጫዎችን አውጥተዋል፣ የእጩዎች መሰረዝን እና በየምዝገባ ቦታ ያሉ ችግሮችን ጠቅሰዋል ፡፡ ዋና ዋናዎቹ የሳምንቱ ከምርጫ ጋር የተያያዙ ክስተቶች የሚከተሉትን ይመስላሉ፡፡
ሰማያዊ ፓርቲ ካስመዘገብኳቸው እጩዎች 200 ያህሉ ተሰርዘውብኛል ያለ ሲሆን እነዚህ እጬዎች ስረዛን አስመልክቶ የምዝገባ ሰራተኞች ከበላይ እንዳመትዘግቡ የሚል ትእዛዝ ስለመጣልን አንመዘግብም ማለታቸውን ሊቀመንበሩ ገልጸዋል፡፡ ምርጫ ቦርድ በበኩሉ ፓርቲው የሌላ ፓርቲ አባላትን በሰማያዊ ስም እያስመዘገቡ መገኘታቸውን እና ያንን ተከትሎ ምዝገባ ላይ ማጣራት አንዲደረግ ትእዛዛ ከማስተላለፍ ውጪ ምንም አይነት ክልከላ አላደረግንም ያለ ሲሆን ትብብር በሚባል ህገ ወጥ አደረጃጀት ተጠቅሞ የሌላ ፓርቲ አባላትን እጩ አድርጎ ማስመዝገብ ህገ ወጥ ነው ብሏል፡፡ ትብብር የሚባል ህጋዊ አሰራረር አንደሌላ የገለጸው ምርጫ ቦርዱ በውሳኔው ላይ ቅሬታ ያላቸው አካላት አግባብነት ያለው የቅሬታ ስርአትን ተከትለው መሄድ ይችላሉ ብለዋል፡፡ የእጩ ምዝገባን አስመልክቶ
ኢህአዴግ – 501 የፓርላማ እና ለክልል ምክር ቤት 1300
መድረክ – 303 ለፓርላማ እና ለክልል ምክር ቤት 800
ኢዴፓ – 280 ለፓርላማ እና ለክልል ምክር ቤት 200 ማቅረባቸው ታውቋል፡፡
ሌላው አስገራሚው ከእጨ ምዝገባ ጋር የተያያዘው ዜና የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር እጣ ስላልደረሳቸው ከእጩነት መሰረዛቸው ነው ፡፡ ይህ አስገራሚ ዜና የተሰማው ከምርጫ ቦርድ ሲሆን በአዲስ አበባ ወረዳ 5 ፈረንሳይ ለጋሲዬን አካባቢ የሚወዳደሩት ኢ/ር ይልቃል ከሌሎች ፓርቲዎች እጩዎች ጋር በእጣ ተወዳድረው እጣ ስላልወጣላቸው መወዳደር አይችሉም ተብለዋል፡፡ በእጣው በወረዳው በሚወዳደሩ እጩዎች መካከል የተደረገ ሲሆን ( ገዥው ፓርቲን ሳይጨምር) እጣው ደረሳቸው ተብለው እጩነታቸው ከጸደቀላቸው ሰዎች መካከል የአዲሱ አንድነት አቶ ትእግስቱ ይገኙበታል፡፡ ኢ/ር ይልቃል ሰማያዊ ህዝቡ ዘንድ የገባ ፓርቲ ስለሆነ ከምርጫ ውጪ ለማድረግ ገዥው ፓርቲ የሚያደርገው ጥረት ነው ብለዋል ፡፡ በተያያዘ ዜና ባለፈው ሳምንት የአንድነት አባላትን አንኳን ደህና መጣችሁ ለማለት በተዘጋጀው ፕሮግራም ላይ የገዥው ፓርቲ ጫና እየጨመረ ሲመጣ ሰላማዊ ትግል ለውጥ እያመጣ ነው ማለት ነው የሚል ንግግር ማድረጋቸው ይታወሳል ፡፡
መድረክ በአባል ድርጅቶቹ አማካኝነት 1186 እጩዎችን አስመዝግቧል።
በኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ፣ 168 ለተወካዮች ምክር ቤት 475 ለክልል ምክር ቤት በኢትዮጵያ ማሕበረ ዴሞክራሲ- ደቡብ ሕብረት አንድነት ፓርቲ፣ 83 ለተወካዮች ምክር ቤት 273 ለክልል ምክር ቤት በአረና ትግራይ ለዴሞክራሲና ሉአላዊነት 33 ተወካዮች ም/ቤት 70 እጩዎች ለክልል ምክር ቤት በሲዳማ አርነት ንቅናቄ 19 ለተወካዮች ምክር ቤት 55 ለክልል ምክር ቤት መስመዝገቡን ገልጻል፡፡
በምርጫው ፕሮግራም መሰረት የምረጡኝ ቅስቀሳ እሁድ የካቲት 15 ቀን በይፋ ይጀመራል ተብሏል፡፡ ቅስቀሳውን ተከትሎ ቲቪ አየር ሰአት አና የሚዲያ ሽፋን የሚጀመር ሲሆን የፓርቲ ተወካዬች ባሉበት የሰአት ድልድል ይፋ ይወጣል ብለዋል ብሮድካስት ባለስልጣንና ምርጫ ቦርድ በጋራ በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል ፡፡ የምረጡኝ ቅስቀሳው ምርጫው ሁለት ቀን እስኪቀረው ድረስ ይቀጥላልም ተብሏል ፡፡
ሰሞኑን የህወሃቱ አቶ አባይ ጸሃይ የአዲስ አበባ ከተማ መስፋፊያ ማስተር ፕላንን አተገባበር ተከትሎ የተቃወሙ አካላትን ልክ እናስገባለን የሚለው ንግግራቸው ከተሰማ በኋላ ከኦሮሞ ፌደራላዊ ኮንግረስ የአለም አቀፍ ድጋፍ ቡድን መግለጫ ሰጥቷል ፡፡ በመግለጫው አቶ አባይ ጻሃይ መንግስታዊ ኃላፊነት በጎደለው ሁኔታ በሕዝብ ላይ የጦርነት እና የዘር ማጥፋት ዘመቻ አዉጀዋል። (መረጃዎች እንደምጠቁሙት
1. ከዚህ ቀደም በተፈፀሙትም የዘር ማጥፋት ወንጀሎች ተጠያቂ ነዉ።
2. የፌዴራሊዝም መርሆችን እና ሕገ፡መንግስቱን በሚፃረር ሁኔታ የክልሎችን ራስን በራስ የማስተዳደር መብት አፍርሰዋል። (የኢፌዴሪ ሕገ፡መንግስት አንቀጽ 50-52)
3. ሕዝብን ያላሳተፈ ውሣኔ በማስተላለፋቸው የኢፌዴሪን ሕገ መንግስት አንቀጽ 8(የሕዝብ ሉዓላዊነትን)፣ የሕዝብ ተሣትፎ – አንቀጽ42(2) እና(4) እንዲሁም 89(6)ንደዋል።
4. የሕዝብ ንቀት አሳይተዋል ብሏል፡፡ ይህ የአለም አቀፍ ድጋፍ ቡድን የኦሮሞ ገበሬዎች የልማት ቅድሚያ ተጠቃሚ እንዲሆኑ እና ያለፍቃዳቸው ሚደረገው ማፈናቀል እንዲቆም አሳስቧል
ሰማያዊ ፓርቲ እና የዘጠኙ ፓርቲዎች ትብብር ምህዳሩን የማስከፈት የሰላማዊ ትግል ሂደቱን ክፍል ሁለት ለማካሄድ ዝግጅቴን አጠናቅቄያለሁ ብሏል፡፡ የካቲት 22 በተመሳሳይ ጊዜ በ15 ከተሞች የሚያደርገው ሰልፍ የዚሁ የነጻነት ትግል አካል እንደሆነ የገለጹ ሲሆን ለዚህ ትግል ህዝቡ ዝግጅት አንዲያደርግም ጠይቀዋል፡፡
የኢዴፓው ፕሬዘዳንት ዶ/ር ጫኔ ከበደ በዚህ ሳምንት መጨረሻ ከሪፓርተር ጋር ባደረጉት ቃለመጠይቅ ፓርቲያቸው ሁለተኛ ዋና ፓርቲ ሆኖ የመሄድ እድሉ የሰፋ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ዶክተር ጫኔ በኢዴፓ እና በሌሎች ፓርቲዎች ልዬነት ላይ ፣ የምርጫ ዝግጅት ላይ እና ፓርቲያቸውና ኢህአዴግ አንዲሁም የፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ጉዳይ ላይ ሰፋ ያለ ቃለ መጠይቅ ሰጥተዋል፡፡ ቃለ መጠይቁ ላይ በዋናነት የሊበራሊዝምን ርእዬተ አለም ዙሪያ ነገሮች እንዲያጠነጥኑ ያደረጉት ፕሬዘዳንቱ የልዬነቶቻቸው መሰረት ርእዬተ አለማዊ ነው ይላሉ፡፡
በመጨረሻም የፓርቲዎች ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ሰው ለመላክ የሚቸገረው ገለልተኛው ምርጫ ቦርድ (ሁለት ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ሰው መላክ አንችልም በሚል ራሳቸው አስገድደው ከጠሩት የፓርቲዎች ጠቅላላ ጉባኤ መቅረታቸው ይታወሳል) የህወሃትን 40ኛ አመት በደማቁ አብሮ አክብሯል፡፡ በዚህ በአል አከባበር የምርጫ ቦርድን ወክለው ሃላፊው ዶ/ር መርጋ በቃና ተገኝተዋል ፡፡