የፍትህና የነፃነት ጥያቄያችን ደም በማፍሰስ አይቀለበስም!!! – ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ የተሰጠ መግለጫ

ፓርቲያችን አንድነት ገዥው ፓርቲ፣ ምርጫ ቦርድና የገዥው ፓርቲ ልሳን በመሆን እያገለገሉ ያሉ ሚዲያዎች በመተባበር ከምርጫ ለማስወጣትና ተለጣፊ አንድነት ለመፍጠር የሚደረገውን ጥረት በመቃወም የተቃውሞ ሰልፍ መጥራቱ የሚታወቅ ነው፡፡

የተቃውሞ ሰልፉን ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም እንደምናከናውን ለአዲስ አበባ መስተዳድር ብናሳውቅም መስተዳድሩ በ12 ሰዓት ውስጥ በፅሁፍ ምላሽ መስጠት ባለመቻሉ ሰልፉ እውቅና አለው፡፡ መስተዳድሩ ግን የተጣለበትን ሃላፊነት ከመወጣት ይልቅ ወደ ጎን በመግፋት የተወሰኑና የማይታወቁ ግለሰቦች ፔቲሽን ተፈራርመው አምጥተዋል በማለት ብዥታ ለመፍጠር ሞክሯል፡፡ ፓርቲያችን ህጉን ጠብቆ ህጋዊ የሆነ ሰልፍ ለማካሄድ ቢሞክርም አሁንም ሃላፊነት በጎደለው ሁኔታ የፓርቲያችን ከፍተኛ አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎች ጭካኔ በተመላበት ሁኔታ ከፍተኛ ድብደባ ተፈፅሞባቸዋል፡፡ በተደጋጋሚ እንዳየነው ፖሊስ ደንብ ማስከበር ሲገባው አድሎ ለፈፀመው አካል በመወገን ድብደባ መፈፀሙ ከወገንተኝነት ያልፀዳ መሆኑን እንድናረጋግጥ አድርጎናል፡፡

ጥያቄያችን አሁንም የፍትህ፣ የእኩልነትና ህግ እንዲጠበቅ የማድረግ ነው፡፡ ገዥው ፓርቲ የመንግስትነት ስልጣኑን በመጠቀም የስልጣን ዘመኑን ለማስረዘም እየከወነ ያለውን ሴራ ማስቆም ነው፡፡ ጥያቄያችን የነፃነትና ያልተሸራረፈ ዴሞክራሲ ይረጋገጥ የሚል ነው፡፡ ጥቄያችን ምርጫ ቦርድ የገዥው ፓርቲ አጋር መሆኑ ቀርቶ ገለልተኛ ሚናውን ይወጣ የሚል ነው፡፡ እነዚህ ጥያቄዎቻችን ደግሞ ደም በማሰስ፤ በድብደባም ሆነ በእስር ፈፅሞ አይቆሙም፡፡ ትግላችን የአንድ ፓርቲ የበላይነት አገዛዝ እስከሚያበቃ ድረስ የሚቀጥል ይሆናል፡፡

በሚቀጥለው ሳምንትም በተለያዩ ከተሞችና በአዲስ አበባ የሰላማዊ ተቃውሞ ድምፃችንን ከፍ አድርገን እናሰማለን፡፡ ትግሉ ይቀጥላል፡፡
ድል የህዝብ ነው!!10153833_587630041337455_4078181881316786241_n

10929013_1025283290832513_36173920361695521_n

10945537_586148308186795_6023333897633994809_n

10906300_1025283240832518_6457036903800580676_n

9804_586148321520127_6529646606074484948_n

960281_1025282780832564_2755564035683057427_n