ሰማያዊ ፓርቲ ምርጫ መግባቱን የሰማሁት ድንገት ነው – አቤ ቶኮቻው
አቤ ቶኮቻው
ሰማያዊ ፓርቲ ምርጫ መግባቱን የሰማሁት ድንገት ነው። የት እንደነበርኩ እግዜር ይወቀው እንጂ ሰለሰማያዊ የማውቀው የመጨረሻው መረጃ የምርጫ ምህዳሩ ሳይሰተካከል ምርጫ ማድረግ ”ዋጋ ዘይብሉ” ነው… የሚለውን ነበር።
ትላንትና ያየሁት ፓርቲዎች እና የምርጫ ምልክቶቻቸውን የያዘ ወረቀት ሰላሳ ዘጠኝ የሚደረሱ ፓርቲዎች ምልክት ተሰጥታቸዋል። እዚህ ላይ የገረመኝ… ከብሄር ፓርቲዎች ውስጥ በኦሮሞ ስም የተመዘገቡ ፓርቲዎች ብዛት የትየለሌ አይደል እንዴ፤ ይሄ በተመሳሳይ ሀሳብ ላይ በርካታ ፓርቲዎችን የመፍጠር ስራ የኢህአዴግዬ ከሆነ እንዴት ስራ በዝቶባት እንደከረመች ለማውቅ አይከብድም።
ለማንኛውም ሰማያዊ ፓርቲ የምርጫ መወዳደሪያ ምልክቱ ዛንጥላ ሆኖ ወደ ምርጫው መግባቱን አረጋግጧል። በርግጥ በተለይ ሰማያዊ መኢአድ እና አንድነት ቢያንስ የየራሳቸው ህልውና ተጠብቆ በተመሳሳይ የምርጫ ምልክት ቢወዳደሩ የሚፈጥሩት ነገር በኔ ግመት ቀላል የማይባል ቢሆንም። ሰማያዊ ምርጫ ሳይገባ ከሚቀር ለውድድር መቅረቡ መልካም ነው እና በርቱ እላቸዋለሁ!!
ምርጫ ቦርድ/ኢአዴግ ለአንድነት እና ለመኢአድ የምርጫ ምልክታቸውን እስካሁን አልሰጣቸውም። ሳስበው በመጀመሪያ በደንብ ስማቸውን ማጥፋት አለብኝ ብሎ ቆርጦ የተነሳ ነው የሚመስለው፤ በኢቲቪ ”አንዳንድ ያዲሳባ ነዋሪዎች” ሳይቀሩ፤ ”መኢአድ እና አንድነት በአመራሮቻቸው መካክል የተፈጠረውን አለመግባባት ቀርፈው… ወደ ምርጫ ቢገቡ…” እያሉ በኢቲቪ አስተያየት እየሰጡ ነው። እኛ ያልሞትን እማኞች እንደምንመሰክረው በመኢአድ እና በአንድነት ውስጥ ምንም የአመራር ሽኩቻ አላየንም፤ በዛኛው በኩል አሉ የሚባሉት የሁለቱም ፓርቲ ሰዎችም አደባባይ ወጥተው ሲናገሩ እና ሲከራከሩ አልሰማንም። በነርሱ ፈንታ የሚናገሩላቸው እና የሚሟገቱላቸው ኢህአዴጎች እና ምርጫ ቦርዶች ናቸው!
ሁለቱ ፓርቲዎች ምርጫ እስካሁን ያልገቡበት ምክንያት እስከሚገባኝ ድርስ ”አናስገባም ሰርገኛ” ተብለው ነው።




