የምርጫ ‹‹ቦርድ›› ነገር፤ – ከዳዊት ሰለሞን

ኢትዮጵያ ውስጥ በህግ ማዕቀፍ ራሱን ችሎ የሚሰራ ነጻ ተቋምን ለማግኘት በየትኛውም የመንግስት አስተዳደር አልታደልንም፡፡ ስርዓቶቹን የመሩና ሚመሩ ባለግዜዎች የፈጠሯቸውን ተቋማት በአንድ የስልክ ጥሪ ሲያሽከረክሩ ቆይተዋል፡፡ምርጫ ቦርድም በአዋጅ ቢቋቋምም የስርዓቱ ሎሌ ከመሆን አልዘለለም፡፡ይህ ተቋም እንደ አንድ ገለልተኛ አካል ‹‹ቦርድ ››እየተባለ እንዲጠራ ከመደረጉ ውጪ ለገዢው ቡድን ዘብ በመቆም ሽንጡን ገትሮ ሲከራከር አድልዎ ሲፈጽምና ኮሮጆ ሲገለብጥ እዚህ ደርሷል፡፡ሁልግዜም የአቅም /የገንዘብና የማቴሪያል/ችግር እንጂ ሌላ ጉድለት ሲያልፍም እንደማይነካው የሚናገረው ምርጫ ‹ቦርድ› አሁን የስንግ ተይዟል፡፡

ምርጫ ‹‹ቦርድን››አጣብቂኝ ውስጥ የመሰገው አንድነት ፓርቲ ነው፡፡የፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ ጠቅላላ ጉባኤ የሚደረገው በብሄራዊ ምክር ቤቱ ጥሪ ሲደረግ አልያም የፓርቲው ኦዲትና ኢንስፔክሽን ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠራ ሲወስን መሆኑን ይደነግጋል፡፡ ባሳለፍነው እሁድ የተወሰኑ ግለሰቦች ባገኙት የገንዘብ፣ የማቴሪያልና የምርጫ ‹ቦርድ›ድጋፍ ጠቅላላ ጉባኤ በአንድነት ስም በማድረግ በነጋው ይህንኑ ለምርጫ ‹ቦርድ›ማሳወቃቸውን የምርጫ ‹ቦርድ›ታዛቢም በስብሰባው መገኘቱን ሰምተናል፡፡

የምርጫ ‹ቦርድ› ህገ ወጥነት
አንድነት በህገ ደንቡ ስለጠቅላላ ጉባኤ አጠራር በማስፈር ይህንኑ ለምርጫ ‹ቦርድ›አሳውቋል፡፡ምርጫ ‹ቦርድ›ም የፓርቲውን ጠቅላላ ጉባኤ የሚመዝነው ከፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ በመነሳት እንጂ በራሱ መንገድ አልያም በእነ በረከት ቀጭን የስልክ መልእክት መሰረት አይደለም፡፡በሆቴል ውስጥ ጠቅላላ ጉባኤ በማድረግ ትዕግስቱን መረጥን ካሉ ሰዎች መካከል ከሶስት የማይበልጡ ሰዎች የአንድነት ብሄራዊ ምክር ቤት አባላት እንደነበሩ ከለጠፉት ፎቶ ግራፍ በቅርበት የሚያውቃቸው ሰው ሊረዳ ይችላል፡፡ሌሎቹ ምንም ያህል ቁጥር ቢኖራቸው ጠቅላላ ጉባኤ ማድረግና መሪ መምረጥ አይችሉም፡፡
በፓርቲ ስም ስብሰባ ለማድረግ የአዲስ አበባ መስተዳድር ከምርጫ ቦርድ የድጋፍ ደብዳቤ እንዲጻፍለት ይጠይቃል፡፡ምርጫ ‹ቦርድ›ለእነዚህ ሰዎች በአንድነት ስም እንዲሰበሰቡ ፈቃድ የሰጣቸው ምን አግኝቶባቸው ይሆን ?

በፓርቲው ውስጥ መርህ ተጥሷል ፣በህገ ወጥ መንገድ ሰዎች ሀላፊነት ወስደዋል ብለው የሚያምኑ ሰዎች ጉዳያቸውን ለኦዲትና ኢንስፔክሽን በማቅረብ ወይም ብሄራዊ ምክር ቤቱ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠራ ፊርማ በማሰባሰብ ኮረም እንዲያስሞሉ ምርጫ ‹ቦርድ›መምከር ሲገባው በስብሰባው ወቅት ታዛቢ መላኩ አመራሮቹን በወንጀል ሊያስጠይቃቸው ይገባ ነበር፡፡
ምርጫ ‹ቦርድ›ባለመኖሩ ግን እነትዕግስቱ ከስብሰባው መልስ ኢቴቪ ላይ ቀርበው ዲስኩር እንዲያሰሙ ነገሮች ተመቻቹላቸው፡፡