‹የተሰበሰበ ድንች›
click here for pdf
ከለም ሆቴል ወደ ካዛንቺስ የሚሄድ ታክሲ ውስጥ ገብቼ ከኋላ ወንበር ተቀመጥኩ፡፡ ከጎኔ ሁለት በዕድሜ ወደ ሠላሳዎቹ አጋማሽ የሚሆኑ ሴቶች ተቀምጠዋል፡፡ ታክሲው ሲንቀሳቀስ ‹‹ለመሆኑ ምን ዓይነት ነገር ቢገጥምሽ ነው ለመንገር ያስቸግራል የምትይኝ›› አለቻት መካከል ያለቺዋ ወደ መስኮቱ ጥግ የተቀመጠችውን፡፡ እንደ ታክሲ መቼም ማኅበራዊ ኑሯችንን የምናውቅበት ምቹ መድረክ የለምና ጆሮዬን ጣል አደረግኩ፡፡ ‹‹ባክሽ ችግሩን ከመሸከሙ ችግሩን መግለጡ ይከብዳል›› አለች ያችኛዋ፡፡
አንድ ሊቅ ‹‹እጅግ አስቸጋሪው ችግር ሊገልጡት የሚያስቸግር ችግር ነው›› ያሉትን አስታወሰኝ፡፡ ምን እንደገጠማት ባላውቅም አንዳንድ ችግር ግን የሕመሙን ያህል መግለጫ ነገር አይገኝለትም፡፡ ሲናሩት ተራ ወይም ቀላል ይሆናል፡፡ ሰሚውም ‹‹አሁን ይኼ ችግር ነው?›› ይላል፡፡ ተናጋሪውም ንግግሩ ቀላል ስለሚሆንበት ከችግሩ በላይ ያመዋል፡፡
‹‹ግዴለሽም እንደምንም ብለሽ ንገሪኝ›› አለቻት፡፡
‹‹አንቺና ባለቤትሽ ስታወሩ እንዴት ነው?›› ስትል ጥያቄዋን በጥያቄ መለሰችው፡፡
‹‹እንዴት?በቃ ማውራት ነዋ፡፡››
‹‹ስታወሩ ምን ይሰማሻል?››
‹‹ፊዚክስ አደረግሽዋኮ›› አለች እየሳቀች፡፡
‹‹እኔ ግን ከእርሱ ጋር ሳወራ ያመኛል፡፡››
‹‹እንዴት? ይሰድብሻል፤ ይቆጣል፤ ምን ዓይነት ክፉ ቃል ቢናገርሽ ነው››
በመስኮቱ ጥግ ያለችው ሴት አንገቷን ስትነቀንቅ በዚህኛው መስኮት ነጸብራቅ በኩል አያታለሁ፡፡
‹‹ሁሉም አይደለም›› አለቻት፡፡ ጠያቂዋ የእፎይታ ትንፋሽ በረጅሙ ተነፈሰች፡፡
‹‹ታድያ ምድን ነው?›› አለች ጠያቂዋ፡፡
‹‹አየሽ ለመናገር አስቸጋሪ የሚሆነው አሁን ካልሻቸው ነገሮች አንዱን እንኳን ስላልሆነ ነው፡፡ እስካሁን ስም የወጣለት አይመስለኝም፡፡ ስድብ አይደለም፤ ቁጣ አይደለም፤ ማመናጨቅ አይደለም፤ ሽሙጥ አይደለም፤ ጭቅጭቅ አይደለም፣ ንትርክ አይደለም፤ ክርክር አይደለም፤ ሌላ ነው››
‹‹እንዴ እንትናዬ(ስሟን እያቆላመጠች) ምንድን ነው የሆንሽው? ምንድን ነው የሚያደርግሽ?››
‹‹የሁለታችን ወሬ ያማል፤ ጣዕም የለውም፡፡ እንጨት እንጨት የሚል፡፡ ምንም ነገር የሌለው፤ በቴፕ ተቀድቶ ብትሰሚው ባልና ሚስት እያወሩ ነው የማትዪው ዓይነት››
ወደራሴ ተመለስኩ፡፡ ‹የሚያም ንግግር› ብላ የጠቀሰችው ምንድን ነው? ስድብ ካልሆነ፣ ግልምጫ ካልሆነ፣ ቁጣ ካልሆነ፣ አግቦ ካልሆነ፣ ክርክር ካልሆነ፣ ጭቅጭቅ ካልሆነ፣ ንትርክ ካልሆነ፣ እንካ ሰላንትያ ካልሆነ፤ ታድያ ምንድን ነው? ‹እንጨት እንጨት የሚል› ያለችው ምንድን ነው?
ሰውን ከሰው ጋር የሚያግባባው ዋናው ነገር ቋንቋ ነው፡፡ ካልተናገረ አይታይ ብልሃቱ፣ ካልታረደ አይታይ ስባቱ የተባለውም ለዚህ ነው፡፡ ከአያያዝ ይቀደዳል፣ ከአነጋገር ይፈረዳል የሚልም ተጨምሮበታል፡፡ ግን መናገር ማለት ምን ማለት ነው? ንግግር ሁሉ መልእክት ያስተላልፋል? ንግግር ሁሉ ያግባባል? ሰው በቋንቋ እንደሚግባባው ሁሉ የማይግባባውም በቋንቋ ነው፡፡ ኤፍሬም እሸቴ ‹‹ቋንቋ መግባቢያ አይደለም›› የሚል ጽሑፍ ነበረው፡፡ ‹ቋንቋ ከሌላቸው እንስሳት በላይ ቋንቋ ያለው ሰው አለ መግባባት ከቻለ ቋንቋ ምኑን መግባቢያ ሆነው› ይላል፡፡
ቋንቋ ግን ብቻውን አያግባባም፡፡ ሐሳብ፣ ቃላት፣ ሰዋስውና ንግግር ብቻቸውን ሰዎችን አያግባቡም፡፡ ብቻቸውንም ውስጣችንን አይገልጡም፡፡ የእጆቻችን ወንጫፊዎች፣ የፊታችን ኩስታሬ፣ የዓይኖቻችን እንቅስቃሴ፣ የድምጻችን ቃና፣ የአንገታችን ንቅናቄ እንኳን ተጨምሮበት በሚፈለገው መጠን ሊያግባባን ዐቅም የሚያንሰው ጊዜ አለ፡፡ በመናገርና በመሰማት መካከል ልዩነት የሚፈጥረው፣ በማስረዳትና በመረዳት መካከል ያለውን ክፍተት የሚያሰፋውና የሚያጠበው፣ በሚወረወረው መልእክትና በሚፈጠረው ምላሽ መካከል ያለውን የተገቢነት ምጣኔ የሚለካው አንዱ ነገር – የቋንቋው ጣዕም ነው፡፡
ልክ እንደ ምግብ ጣዕም፡፡ አንድ ሰው አንድን ምግብ ለጤና ተስማሚ፣ የተመጣጠነ ምግብ የያዘ፣ በውድ ዋጋ የተገዛ ስለሆነ ብቻ አይመገበውም፡፡ እጅ የሚያስቆረጥም፣ ምላስ የሚያስቀረጥፍ፣ ሰሐኑን ብሉት ብሉት የሚያሰኝ የሚባልለት ሌላ ነገር ያስፈልገዋል – ጣዕም፡፡ ከአሠራሩ፣ ከይዘቱ፣ ከቁሌቱ፣ ከቅመሙ፣ ከውሕደቱ፣ ከአበሳሰሉ፣ ከቅንብሩ የሚመጣ፡፡ ለዚህም ነው መጋቢዎችና አስመጋቢዎች ከምግቡ ይዘት ባሻገር ለምግቡ ጣዕምና ለምግቡም አቀራረብ የሚጨነቁት፡፡ በምግብ ሂደት አንዱ ወሳኝ ነገር በምግቡና በበላተኛው መካከል ያለው ክፍተት ነው፡፡ በላተኛውን ወደ ምግቡ የሚወስደው፣ ያንን ምግብ እንዲመርጥ፣ ከመረጠም በኋላ ወዶትና ጣፍጦት እንዲበላ የሚያደርገው ነገር ነው – ይኼ በምግብና በበላተኛ መካከል ያለው ነገር፡፡ የገዛነውን ሁሉ ወደ ሆዳችን አንልከውምኮ፤ ገዝተነው የማንበላው ምግብ አለ፡፡
ከፍትፍቱ ፊቱ የሚለው ነገርኮ እንዲሁ አልመጣም፡፡ ያ ሁሉ ጣዕም ያለው ምግብ ቢዘጋጅ እንኳን ‹‹ብሉልኝ፣ ጠጡልኝ፣ በሞቴ፣ አፈር ስሆን፣›› እያለ ጠብ እርግፍ ብሎ የሚጋብዝ፣ ፊቱ ለምግብ የተፈጠረ ጋባዥ ካላገኘ ያቅራል ማለት ነው፡፡ ‹ሲያዩት ያላማረ ሲበሉት ያቅራል› እንዲሉ፡፡ እስኪ አስቡት እንደ ድሮ የአንደኛ ክፍል አለቃ፣ አርጩሜ ይዞ የተኮሳተረና ‹ብላ! አርፈህ ብላ! ውሰድ! ከቀይ ወጡ ውሰድ! አልጫ ጨመር! ዋ!›› የሚል አስተናጋጅ ከጎኑ የቆመበት ግብዣ ቢገጥማችሁ እንዴት ነው የሚበላችሁ፡፡
ንግግርም እንደዚያው ነው፡፡ ቀልዶች፣ ምሳሌዎች፣ ሰምና ወርቆች፣ አባባሎች፣ ግጥሞች፣ ተረቶች፣ ዘይቤዎች የተፈጠሩት ቃላት ቃላት ስለሆኑ ብቻ የልባችንን ስለማይገልጡት ነው፡፡ የንግግር ዜማ፣ የአወራር ዘይቤ፣ የአገላለጥ መንገድ፣ የነገር ክዋኔና የአነጋገር ቃና ንግግሩ እንዲሰማ ሳይሆን እንዲበላ ያደርገዋል፡፡ ከሆድ ጠብ እንዲል፣ አንጀት እንዲያላውስ፣ ቁጣን አቀዝቅዞ፣ ፈገግታ እንዲጨምር፣ ኀዘንን አስረስቶ ደስታን እንዲያስከትል ያስችለዋል፡፡
ያቺ በመስኮቱ ጥግ የነበረችው ሴት እንዲህ ብላ ነበር ለጓደኛዋ ምሳሌ የሰጠቻት፡፡
ዛሬ ጠዋት የተነጋገርነውን ነገር ልንገርሽ፡፡
ደወለና ‹ልጆቹን ዛሬ ማነው ከትምህርት ቤት የሚያወጣቸው?›
‹አንተ አትችልም እንዴ?›
‹አልችልም›
‹ምን ይሻላል?›
‹እንትና ያውጣቸው ንገሪው›
‹አንተ ብትደውልለት አይሻልም?›
‹አንቺ ደውዪ›
‹ስልኩን ትሰጠኝ?›
‹ቴክስት አደርጋለሁ›
‹ኦኬ›
‹ቻዎ›
አሁን እዚህ ውስጥ ፍቅር፣ ናፍቆት፣ ደግነት፣ ቤተሰባዊነት፣ ኀዘኔታ፣ አክብሮት፣ ባልነት፣ ሚስትነት አሉ? አሁን ይኼ ንግግር በሁለት አማርኛ በሚችሉ ሰዎች መካከል የተደረገ መሆኑን እንጂ በሚዋደዱ ባልና ሚስት መካከል የተደረገ መሆኑን የሚያሳይ አንዳች ነገር ልታሳዪኝ ትችያለሽ፡፡ እንዲህ ነውኮ ሁሌም የምናወራው፡፡ ቃላት መለዋወጥ ብቻ፡፡ ዜማ የለው፣ ፍቅር የለው፣ አክብሮት የለው፣ ትኅትና የለው፣ ናፍቆት የለው፡፡ ባዶ ቃላት ብቻ፡፡ የተሰበሰበ ድንች፡፡
‹የተሰበሰበ ድንች› ነበር ያልኩት ለራሴ፡፡ ‹እምቦቲቶ› ሲበላ እንኳን በሚንተከተክ ብረት ድስት ተቀቅሎ፣ በሚጥሚጣ፣ በቁንዶ በርበሬ፣ በጨው ጣፍጦ ነው፡፡ ‹የተሰበሰበ ድንች› አለች፡፡ አንድ የቢሮ ጓደኛዬ ምን እንዳለችኝ ልንገርሽ.. ስትል የመውረጃ ቦታችን ደረስን፡፡ – ካዛንቺስ፡፡ ወረድን፡፡ ወደ ኡራኤል አቅጣጫ እየወረዱ ተረከችላት፡፡
(ይቀጥላል)