ጊዜ ያለፈበት ንስሃ
ጊዜ ያለፈበት ንስሃ
(የሌተናንት ኮሎኔል መንግሥቱ ኃ/ማርያም ትዝታዎች)
አንድ ጥይትና አንድ ሰው እስኪቀር እናት ሃገር ወይም ሞት እያሉ ሲያፋክሩን የነበሩት ቆራጡ መሪአችን ዛሬ ጥይትም ፉከራም አልቆባችው ራሳቸውን በዝምባቢዌ ካስጠለሉ ዘመናት አልፈዋል። አልፎ አልፎ ወሪያችው ብቅ ሲልና እሳቸውም ሲያወሩልን እከታተላለሁ። በሁለት ጥራዝ ለፍጆታ ያህል የቀረበልንንም የትዝታ ስብሰብ ተመልክቸዋለሁ። እዚህ ግባ የሚባል ነገር የለበትም። እንደ ልጆች የዕቃ ዕቃ ጭዋታ ያደረ እንጀራ ቁርስርስ ጫዋታ ፍርስርስ እንደማለት እንጂ። ከዚህ ላይ ግን የትዝታ አቀናባረዋን ትጋትና ብርታት አደንቃለሁ። የመጽሃፉ ይዘትና ብቃት የኮሎኔሉ ቅዥት በመሆኑ አስተያየቴ ጸሃፊዋን አይመለከትም።
አስተናግር እንደበላ ሰው የቆጥ የባጡን የሚቀባጥሩት የቀድሞው መሪያችን ራስን ንጽህ ለማድረግ የቆመንና ያለፈን እየወቀሱ የራሳቸውን ያለፈ የፓለቲካ እድል ፈንታ ለማሳመር መከጀል ትንጋሎ እንደመትፋት ነው። እውኑን የኢትዮጵያ ህዝብ ያውቃልና። ያቺ ውብ ሃገር ከአፍራሽ ወደ አፍራሽ እንድትሽጋገር ያደረጋት የርሳቸው ግትራዊ አመራር ነው። ትላንት ዛሬ አይደለምና የቅጥፈት ፕሮፓጋንዳውን በመተው ያለፈንና ያሁኑን እውነተኛ ታሪክ በራሳቸው በዕር በመጎፈጫጨር ከሐረር እስከ ሃራሬ ያለውን አንዳችም ሳይቀር ለታሪክ ተተው ቢያልፉ ንስሃቸው ሰሚ ያገኛል።
በጊዜው የውጭ የዜና አውታሮች እንዳናፈሱት ኮሎኔሉ የማዳመጥ ችሎታ ያላችው፡ የተነገራቸውን የማይረሱ እንደሆኑ ዘግበዋል። እጎናቸው ሆነው ያዘው ጥለፈ ሲሉ የነበሩም ይህን ባህሪያቸውን መስክረዋል። በመሆኑም በአስራሰባቱ ዓመታት የተፈጸሙ ድርጊቶችን አንድም ሳያስቀሩ ቢያካፍሉን ለመኖር ለገደሉ፤ ጀምላ እስራትና ግርፋት ለደረስብን፤ ከሞት ተርፈን ያለልባችን በባእድ ሃገር ለምንኖር፤ የሳቸውን ስንኩል አመራር አምነው ለውድ ሃገራቸው በየበረሃው በጠላት ጥይት ለረገፉና አሁን ደግሞ በወያኔ ግፍና መከራ በየስርቻው ተጥለው ለሚማቅቁ ሁሉ ከሃውልት የላቀ መታሰቢያ ይሆናል።
ከዚህ ወጭ ጌዜው ያለፈበት ንስሃ ለዛውም በሰማ በለው መናዘዝ ለምህረት አያበቃም። የኢትዮጵያ ህዝም መስማት የሚፈለገው እውነቱን ከሳቸው አንደበትና በራሳቸው ብዕር ያቀለሙትን መጣጥፍ ነው። ብለየር ቶሞሰን (Blair Thomson) Ethiopia, the Country That Cut Off Its Head: A Diary of the Revolution በተሰኘው መጽሃፉ ሊያመላክተን እንደከጀለው ዝም ብሎ አንገት አልባ እስክስታ ላሳያቹህ ማለት በቆመና በሙታን መቀለድ ነው። ኮሎኔሉና በዙሪያቸው የነበሩ ሁሉ ራስን ለማዳን ከመመጻደቅ ይልቅ በትዝታ ፈረስ ተሳፍረው ያለፈን የትግል እሰጣ – ገባና ጭፍን ግብግብ እውነቱን ብቻ በመጣጥፍ መልክ ተተውለን ቢያልፉ ልብ ያለው ይማርበታል አልፎ ተርፎም እንወዳታለን ለሚሉት ያ መከረኛ ህዝብና ሃገርም ታላቅ ስጦታ ነው።
ለዛሬው ይብቃኝ፡
ሰንበተን እንይ!!
አደፍርስ ተሰማ
ከሚኒሶታ