ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች አመራሮች ጋር ተወያዩ

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች አመራሮች ጋር ተወያዩ

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ላይ ከአገር አቀፍ ፓርቲዎች አመራሮች ጋር ውይይት አደረጉ፡፡

ባለፈው ዓርብና ቅዳሜ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክስ ኮሚሽን አዳራሽ በተካሄደ ስብሰባ ላይ ጥሪ የተደረገላቸው 22 የፖለቲካ ፓርቲዎች በውይይቱ ላይ ተሳትፈዋል፡፡ የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ (መድረክ) እና ሰማያዊ ፓርቲ ‘በዕድገትና በልማት አጀንዳዎች ላይ ከመወያየታችን በፊት፣ በሌሎች አጠቃላይ ፖለቲካዊና አገራዊ ጉዳዮች ላይ መወያየት መቅደም አለበት’ በማለት በስብሰባው እንደማይካፈሉ በማስታወቃቸው በአዳራሹ ሳይገኙ ቀርተዋል፡፡ ባለፈው ዓርብ  በመጀመሪያው የዕድገትና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ አፈጻጸም ላይ በሚኒስቴር ዴኤታ ማዕረግ የብሔራዊ የፕላን ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ ጌታቸው አደም አማካይነት ማብራሪያ የቀረበ ሲሆን፣ በዕቅዱ አጠቃላይ አፈጻጸሞችና ጉድለቶች ላይ ከተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችና ከተሳታፊዎች ለተነሱ ጥያቄዎች፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ምላሽ ሰጥተዋል፡፡