በአያት ሁለት ኮንዶሚኒየም ያልተከደነ ቱቦ የሰው ሕይወት አጠፋ

በተለምዶ አያት አደባባይ እየተባለ በሚጠራው አያት ቁጥር ሁለት ኮንዶሚኒየም አካባቢ፣ ባልተከደነ ቱቦ ምክንያት የአራት ዓመት ሕፃን ሕይወት መስከረም 5 ቀን 2008 ዓ.ም. አለፈ፡፡
በአካባቢው በሚገኙት ኮንዶሚኒየም ቤቶች ውስጥ በአብዛኛው የሚኖሩት በመልሶ ማልማት ከአራት ኪሎና ከተለያዩ አካባቢዎች የተነሱ ነዋሪዎች ሲሆኑ፣ አደጋው የደረሰው ከእነዚህ መካከል አንዱ በሆኑት አቶ እንግዱ ዘለቀ ሕፃን ልጅ ላይ ነው፡፡
የሕፃኑ ሕይወት የተቀጠፈውም የቤቶቹ ግንባታ ባለመጠናቀቁና የተከፈቱ ቱቦዎች በመኖራቸው እንደሆነ ቤተሰቦቹ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
የሟች ሕፃን አጐት አቶ አበበ ለውጠኝ ስለጉዳዩ ተጠይቀው በሰጡት ምላሽ፣ አካባቢው ለመኖሪያ በጣም አደገኛ እንደሆነና በየቦታው ተቆፍረው ያልተከደኑ ቱቦዎች በብዛት አሉ ብለዋል፡፡ ከእነዚህም አንዱ ሟች ሕፃን ኢዮብ እንግዱ የገባበት ቱቦ ሦስት ሜትር ጥልቀት እንዳለውና ከመኖሪያ ቤታቸው ጀርባ እንደሚገኝ አመልክተዋል፡፡
ሕፃኑ ጠፋ ተብሎ ሲፈለግ ከቆየ ከአንድ ሰዓት ፍለጋ በኋላ ወደ ቤታቸው ሲመለሱ አስከሬኑ ቱቦው ውስጥ ተንሳፎ እንዳገኙትም ገልጸዋል፡፡
የሟች ሕፃን ወላጆች በድንጋጤ ምክንያት ሰውን ማናገር እንደማይችሉም አቶ አበበ አክለው ገልጸዋል፡፡ በጉዳዩ ላይ የአካባቢው ኅብረተሰብ መስከረም 7 ቀን 2008 ዓ.ም. ሰላማዊ ሠልፍ ማድረጉን ለማወቅ ተችሏል፡፡ ጉዳዩንም ፖሊስ ይዞታል፡፡ የሟች ሕፃን ኢዮብ የቀብር ሥነ ሥርዓት መስከረም 6 ቀን 2008 ዓ.ም. በአባ ኪሮስ ቤተ ክርስቲያን ተፈጽሟል፡፡