ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ: የአድባራት እና የሀገረ ስብከት መዝባሪ ሓላፊዎች በሕግ እንዲጠየቁ መመሪያ ሰጡ
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ ከሢመተ ፕትርክናቸው በኋላ የመጀመሪያ በኾነው የግንቦት ፳፻፭ ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ መክፈቻ ንግግራቸው÷ ፀረ ሙስና ሥርዐት ከተደነገገ ሙስና ይጠፋል፤ ቤተ ክርስቲያን ሕይወት ታገኛለች፤ በማለት አስቸኳይ ርምጃ እንዲወሰድ ጠይቀው ነበር፡፡ ርምጃው ካህናትንና ምእመናንን በማስተባባር የሚፈጸም፣ ቆራጥነትን የሚጠይቅ እና በይዘቱም ሥር ነቀል መኾን እንደሚገባው አመልክተው ነበር፡፡ፓትርያርኩ፣ ቤተ ክርስቲያንን ለመታደግ ተግባራዊ እንዲኾኑ ካሳሰቧቸው ሦስት ዐበይት የለውጥ ርምጃዎች አንዱ የፀረ ሙስና ዓቢይ ኮሚቴ መቋቋም ነው፡፡ ኮሚቴው ኹኔታውን በፍትሐዊነት እየመረመረ ስንዴውን ከእንክርዳድ ለይቶ የማቅረብ እና እንክርዳድ ኾነው በሚገኙት ላይ አስተማሪ እና ሕጋዊ ርምጃ በመውሰድ ብልሹ አሠራርን የማረም እና የማስወገድ ድርሻ ነበረው፡፡
ሥር ሰዶ የሚታየው አሳፋሪ እና አሳዛኝ ብልሹ አሠራር ሳይታረም ቢቀጥል ቤተ ክርስቲያን ችግር ውስጥ እንደምትወድቅ በግልጽ እየታየ እንደኾነ ፓትርያርኩ አመልክተው፣ ‹‹በአጭር ጊዜ ተፈላጊውን ለውጥ ለማምጣት የሚያዳግት ቢኾንም የለውጡን መሠረት በአስቸኳይ ማስቀመጥ እና አቅጣጫውን መቀየስ እጅግ አስፈላጊ ነው፤›› ብለው ነበር፡፡
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የመሬት፣ የሕንጻ እና የልዩ ልዩ ገቢ ማስገኛ ተቋማት የኪራይ ተመንን በማስመልከት የወጣው ጥናታዊ ሪፖርት፣ በጥቂት አማሳኝ የአድባራት ሓላፊዎች እና ግለሰብ ነጋዴዎች የጥቅም ትስስር ቤተ ክርስቲያን በገዛ ሀብቷ እና ንብረቷ የበይ ተመልካች መኾኗን በተጨባጭ ያረጋገጠ ኾኗል፡፡
ሪፖርቱ ባለፈው ረቡዕ፣ የጠቅላይ ጽ/ቤቱ የአስተዳደር ጉባኤ ካሳለፈው ውሳኔ ጋር ለብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ቀርቦ በንባብ በተሰማበት ወቅት በእጅጉ አዝነዋል፡፡ የሕግ ጥሰት እና ምዝበራ በአድባራት የተፈጸመ ቢኾንም ሕግን ማስከበር የሚገባው የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትም ሕግ አስፈጻሚ መኾን ባለመቻሉ የሕግ ጥሰቱ አካል እንደኾነ በሪፖርቱ ተጠቅሷል፡፡
ለውሳኔዎቹ ተፈጻሚነት አጽንዖት የሰጡት ቅዱስነታቸው፣ በጥናቱ የታዩ የአሠራር ጥሰቶችን የሚያረጋግጡ ከ1500 በላይ የሰነድ ማስረጃዎች እንደተሰበሰቡ በቡድኑ በመገለጹ ሕጋዊ ርምጃው እንዲቀጥል መመሪያ ሰጥተዋል፡፡
ሙስና እና ብልሹ አሠራር ከቤተ ክርስቲያናችን ክብር እና ቅድስና ጋር የማይጣጣም በመኾኑ በፍጹም መታየት እንደሌለበት አዘውትረው ከመናገራቸው አንጻር የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ አመራር ቢዘገይም ፈጽሞ ከመቅረቱ ይሻላልና ተግባራዊነቱ ተጠናክሮ መቀጠል ይኖርበታል፡፡ የፀረ ሙስና ሥርዐቱን በመደንገግ የለውጡን መሠረት የሚያስቀምጥ፣ አቅጣጫውንም የሚቀይስ ነውና!
* * *
(አዲስ አድማስ፤ ቅጽ ፲፭ ቁጥር ፰፻፲፪፤ ቅዳሜ ነሐሴ ፪ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም.)
- ከ1500 በላይ የሰነድ ማስረጃዎች፣ በመቶዎች የሚቆጠሩ የሰው ምስክሮች ተዘጋጅተዋል
- መረጃ በመስጠታቸው የታገዱና የተዛወሩ ሓላፊዎች ወደ ቦታቸው እንዲመለሱ ተወስኗል
- የአድባራትን ሕንጻዎች የሚያስተዳድር ጽ/ቤት እና በበላይነት የሚመራ ቦርድ ይቋቋማል
- ‹‹በመዝባሪ ላይ አልደራደርም፤ እስከ መጨረሻው ከፊት ለፊት ነኝ›› /ፓትርያርኩ/
በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የአድባራቱን ሰፋፊ መሬቶች እና የገቢ ማስገኛ ተቋማት እየመዘበሩ ራሳቸውን ያበለጸጉ የአድባራት እና የሀገረ ስብከት የአስተዳደር ሓላፊዎች በሕግ እንዲጠየቁ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ መመሪያ ሰጡ፡፡
የአስተዳደር ሓላፊዎቹ የአድባራቱን ሰፋፊ መሬቶች እና የንግድ ተቋማት ያለጨረታ ከገበያ ዋጋ በታች ከ15 ዓመት እስከ ዕድሜ ልክ በመዋዋል የቤተ ክርስቲያኒቱን ጥቅሞች አሳልፈው በመስጠት ራሳቸውን አበልጽገዋል፡፡
ፓትርያርኩ መመሪያውን የሰጡት፣ ላለፉት ስምንት ወራት በሀገረ ስብከቱ አድባራት እና አንዳንድ ገዳማት የመሬት፣ የሕንፃ እና የልዩ ልዩ ገቢ ማስገኛ ተቋማት ኪራይ ተመንን ሲያጣራ የቆየው ኮሚቴ ያዘጋጀው ጥናታዊ ሪፖርት ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤቱ የአስተዳደር ጉባኤ የውሳኔ ሐሳብ ጋር ባለፈው ረቡዕ፣ ሐምሌ ፳፱ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. ከቀረበላቸው በኋላ ነው፡፡
በፓትርያርኩ መመሪያ የተቋቋመው ኮሚቴው፣ በ58 አድባራት መሬት፣ ሕንፃ እና ሕንፃ ነክ ጉዳዮች ላይ ባካሔደው ጥናት የተጠቆሙት የመፍትሔ ሐሳቦች እና በብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁ አቡነ ማቴዎስ ሰብሳቢነት የሚመራው የአስተዳደር ጉባኤ የተስማማባቸው የመፍትሔ ሐሳቦች በሙሉ ተፈጻሚ እንዲኾኑ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ትእዛዝ ሰጥተዋል፡፡
በጥናቱ ሒደት የኮሚቴውን አባላት በጥቅም ለመደለል ከመሞከር ጀምሮ በማስፈራራት፣ ስም በማጥፋት እና ሰነዶችን በመደበቅ የማጣራት ሥራውን ለማስተጓጐል ሲጥሩ የነበሩ ሐላፊዎች፣ በመፍትሔው አተገባበር ላይም ዕንቅፋት ሊፈጥሩ ይችላሉ ለሚለው ስጋት ፓትርያርኩ በሰጡት ምላሽ፤ ‹‹ወደ ኋላ ወደ ጎን የለም፤ ወደፊት ነው፤ በቤተ ክርስቲያን ሀብት ምዝበራ ከማንም ጋር አልደራደርም፤ ከጎኔ ኹኑ፤ እስከ መጨረሻው ከፊት ለፊት ነኝ›› ሲሉ በቁርጠኝነት ተናግረዋል፡፡
በጥናታዊ ሪፖርቱ እንደቀረበው፤ ለልማት የተሰጡት የአድባራቱ መሬቶች፣ ከአዲስ አበባ የመሬት ገበያ አንጻር ሊታሰብ ከማይችልበት ዝቅተኛው በካሬ ሜትር 0.37 ሳንቲም፣ ከፍተኛው ብር 70 ያለጨረታ ከ15 ዓመት እስከ ዕድሜ ልክ የኪራይ ውል ተፈጽሞባቸዋል፡፡ ይህም ጥቂት አማሳኝ የደብር ሓላፊዎች እና ግለሰብ ነጋዴዎች ሚልየነር እንዲኾኑበት ዕድል በመስጠት ቤተ ክርስቲያኒቱን የበይ ተመልካች እንዳደረጋት ተገልጧል፡፡
የአድባራት አለቆች፣ ጸሐፊዎች፣ ሒሳብ ሹሞች፣ ተቆጣጣሪዎች እና የሰበካ ጉባኤ አባላት በተገኙበት በተካሔደው ማጣራት፣ ለጥናት ቡድኑ መረጃ በመስጠታቸው እና ብልሹ አሠራሮችን በመቃወም ጥያቄ በማንሣታቸው ከመመሪያ ውጭ ከሓላፊነታቸው የታገዱት፣ የመናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ደብር ዋና ተቆጣጣሪ መጋቤ ጥበብ ወርቁ አየለ እና የደብረ ጽጌ ቅዱስ ዑራኤል ቤተ ክርስቲያን ዋና ሒሳብ ሹም ወ/ሮ መና የማነ ብርሃን ሥዩም ወደ ቀድሞ ሓላፊነታቸው እና ቦታቸው እንዲመለሱ በአስተዳደር ጉባኤው ተወስኗል፡፡
የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የሕግ አገልግሎት መምሪያ፤ አማሳኝ ሓላፊዎችን ለሕግ ከማቅረብ በተጨማሪ የገቢ ማስገኛ ተቋማቱ በተከራዮች ለሦስተኛ ወገን በከፍተኛ ዋጋ እየተላለፉ የተሰጡባቸውን ውሎች በመሰረዝ የቤተ ክርስቲያኒቱን ጥቅም የሚያስከብር እና የሚያስቀድም ወጥ አሠራር እንዲዘረጋ ተወስኗል፡፡
የአድባራቱ ሕንፃዎች እና መሬቶች በየአጥቢያው በተናጠል የሚተዳደሩበት አካሔድ ቀርቶ በማእከል የሚመሩበት ሥርዐት እንደሚበጅ የተጠቆመ ሲኾን ይህን የሚያስፈጽም ጽ/ቤትና በበላይነት የሚመራ ፓትርያርኩ የሚሰበስቡት ቦርድ እንደሚቋቋም ታውቋል፡፡
የፓትርያርኩ ልዩ ሀገረ ስብከት በኾነው አዲስ አበባ፣ ጥናቱ ባልሸፈናቸው ሌሎች አድባራት እና ገዳማትም እንዲቀጥል ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ያዘዙ ሲኾን በመጪው ዓመት ጥቅምት በሚካሔደው ፴፬ኛው ዓመታዊ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤም በአገር አቀፍ ደረጃ እንዲተገበር በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ እንዲወሰንበት እንደሚያደርጉም አስታውቀዋል፡፡
