ሁለት የስኳር ፋብሪካዎች በስድስት ወራት ውስጥ የሙከራ ምርት እንደሚጀምሩ ይጠበቃል

ሁለት የስኳር ፋብሪካዎች በስድስት ወራት ውስጥ የሙከራ ምርት እንደሚጀምሩ ይጠበቃል

ዳንጎቴ የምርት ማሸጊያ ፋብሪካ ለመገንባት ጠይቋል 

ሦስት የስኳር ፋብሪካዎች የሙከራ ምርት መጀመራቸውን በማስመልከት ለሪፖርተር ማብራረሪያ የሰጡት የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ አብተው፣ ከሰም ስኳር ፋብሪካ ሙሉ ለሙሉ የሙከራ ሥራ መጀመሩንና በቅርቡም ወደ ዋናው የምርት ሒደት እንደሚገባ ገለጹ፡፡ 

በከፊል የሙከራ ምርት ከጀመሩት ውስጥ የተንዳንሆና የኩራዝ ስኳር ፋብሪካዎችም ከሦስት እስከ ስድስት ወራት ባለው ጊዜ ውስጥ ወደ ሙከራ ተግባር ይገባሉ ብለዋል፡፡ የከሰም ስኳር ፋብሪካ በቀን እስከ 10,000 ቶን አገዳ የመፍጨት አቅም እንዳለው የገለጹት አቶ አህመድ፣ ሆኖም በአሁኑ ወቅት 6,000 ቶን አገዳ በቀን በመፍጨት ሙከራ እንደሚጀምር አስታውቀዋል፡፡ እንደ ስኳር ኮርፖሬሽን መረጃ ከሆነ፣ የከሰም ስኳር ፋብሪካ በ20,000 ሔክታር መሬት ላይ የተንጣለለና በመስኖ ውኃ የሚለማ የአገዳ እርሻ አለው፡፡ 153 ሺሕ ቶን ስኳር፣ 12,500 ሜትር ኩብ ኤታኖል ሥራ በሚጀመርበት ወቅት እንደሚያመርት የሚጠበቅ ፕሮጀክት ነው፡፡ በሙሉ አቅሙ ማምረት ሲጀምር 260 ሺሕ ቶን ስኳርና 30,000 ሜትር ኩብ ኢታኖል፣ እንዲሁም 15 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል ያመነጫል ተብሎ ይጠበቃል፡፡  

የተንዳሆ ስኳር ፋብሪካ በሁለት ምዕራፍ ግንባታው እተካሄደ መሆኑን የገለጹት  አቶ አህመድ፣ በጠቅላላው 26 ሺሕ ቶን አገዳ በቀን የመፍጨት አቅም እንዳለውና በመጀመርያው ምዕራፍ 13,000 ቶን አገዳ በቀን ይፈጫል ተብሎ ይጠበቃል ብለዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ወደ ሙከራ እየገባ ያለው በስድስት ሺሕ ቶን አገዳ ይጀምራል ተብሏል፡፡ ይህ የሆነውም የተርባይንና የእንፋሎት ሥራዎች ስለሚቀሩ እንደሆነም ተገልጿል፡፡ ከሦስት እስከ ስድስት ወራት ባለው ጊዜ ውስጥ ለሙከራ የሚያበቃው ሥራ ተጠናቆ ምርት እንደሚጀምር ይጠበቃል፡፡

  ሆኖም ተንዳሆ የሚያመርተው 63 ሺሕ ሜትር ኩብ የኢታኖል ምርት ለኢንዱስትሪዎች ፍጆታ ሊውል መታሰቡን አቶ አህመድ ገልጸዋል፡፡ በኬሚካል አምራችነት የተሰማሩ የውጭ ኩባንያዎችና የከብት መኖ በማምረት ላይ የሚገኙ ፋብሪካዎች ኢታኖል እንዲቀርብላቸው በመጠየቃቸው የተንዳሆ ኢታኖል ምርት ለእነዚህ እንደሚውል አስታውቀዋል፡፡ 

በአገሪቱ እስካሁን እየተመረተ የሚገኘው ዓመታዊ የስኳር ምርት መጠን 300 ሺሕ ቶን እንደሆነ የሚገልጸው ስኳር ኮርፖሬሽን፣ ይህንን መጠን ወደ 2.25 ሚሊዮን ቶን ለማድረስ እየሠራ እንደሚገኝ፣ በአሁኑ ወቅት እየተመረተ የሚገኘውን 18 ሚሊዮን ሊትር ኢታኖል ወደ 44 ሚሊዮን ሜትር ኩብ የማሳደግ ዕቅድ መያዙን ሲገልጽ ቆይቷል፡፡ ሆኖም አገሪቱ ከ137 ሚሊዮን ሜትር ኩብ በላይ ኢታኖል የማምረት አቅም እንዳላት ይፋ አድርጓል፡፡ አምስት የስኳር ፋብሪካዎች ይኖሩታል የተባለውን የኩራዝ ፕሮጀክትን ጨምሮ፣ የወልቃይትና የጣና በለስ ስኳር ልማት ፕሮጀክቶች በግንባታ ላይ እንደሚገኙ ይታወቃል፡፡ 

በሌላ በኩል በስኳር ኢንዱስትሪው ውስጥ ይሳተፋሉ ከሚጠበቁ የአገር ውስጥና የውጭ ኩባንዎች እስካሁን ያልተሳካለቸው ሲኖሩ፣ በቅርቡ በሲሚንቶ ምርት ላይ በመሰማራት ሥራ የጀመረው ዳንጎቴ ግሩፕ በስኳር ልማት እንደሚሳተፍ ማስታወቁ አይዘነጋም፡፡ አቶ አህመድ እንደሚሉት የናይጄሪያው ቢሊየነር አሊኮ ዳንጎቴ፣ በስኳር ልማት ለመሰማራት የሚያስችላቸውን ጥናት እያካሄዱ ሲሆን፣ የምርት ማሸጊያ ፋብሪካ ለመገንባት በእንቅስቃሴ ላይ መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡