አንድነት ፓርቲ በደብረማርቆስ ከተማ የተቃውሞ ሰልፋ አካሄደ
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ በደብረማርቆስ ከተማ በዛሬው ዕለት የተቃውሞ ሰልፍ አካሄደ፡፡
አንድነት በዛሬው ዕለት መነሻውን ከደብረማርቆስ ዩኒቨርስቲ መድረሻውን ደግሞ የንጉስ ተክለሀይማኖት ቤተመንግስት ከሚገኝበት ተክለሀይማኖት አደባባይ ያደረገ የተቃውሞ ሰልፍ አካሄዷል፡፡ ፓርቲው ባደረገው የተቃውሞ ሰልፍ ላይ የፓርቲው አባላት፣ ደጋፊዎች እና የደብረማርቆስ ከተማ ነዋሪዎች የተገኙ ሲሆን በሰልፉ ላይ የተገኙት ታዳሚዎችም ምርጫ ቦርድና ገዢው ፓርቲ አንድነትን ለማፍረስ የሸረቡትን ሴራ አውግዟል፡፡
በሰልፉ ላይ በርካታ መፈክሮች የተስተጋቢ ሲሆን ከእነዚህም መሐል በሕዝብ ላይ ፍርሐትን ማንገስ የአምባገነንነት መገለጫ ነው፣ አንድነት አንድ ነው፣ ምርጫ ቦርድ ለገዢው ፓርቲ እያሳየ የሚገኘውን ወገንተኝነት ያቁም፣ አንድነት የህዝብ ነው፣ ሬዲዮ ፋና እና ኢቲቪ በህዝብ ላይ ውዥንብር ለመፍጠር እየሰሩ የሚገኙትን ደባ እንቃወማለን እና ሌሎች መፈክሮችም በስፋት ተስተጋብተውበታል፡፡
በእለቱ በተቃውሞ ሰልፉ ላይ ለተገኙት ታዳሚዎች የአንድነት ፓርቲ ብሔራዊ ምክር ቤት አባል አቶ ዳዊት አስራደና የአንድነት ፓርቲ የምስራቅ ጎጃም ሰብሳቢ አቶ አየነው ተመስገን በሰልፉ መጠናቀቂያ ቦታ በሆነው ተክለሀይማኖት አደባባይ የመዝጊያ ንግግር አድርገዋል፡፡
የፓርቲው ብሔራዊ ምክር ቤት አባል የሆኑት አቶ ዳዊት አስራደ ሰልፉን በማስመልከት ለሚሊየኖች ድምፅ ሲገልፁ ‹‹የህዝቡን የቁርጠኝነት ደረጃ ያሳየ ስኬታማ የተቃውሞ ሰልፍ ማካሄድ እንደተቻለ አውስተው ለህዝቡ ሊተላለፍ የሚገባው መልዕክት በአግባቡ መተላለፉን›› ገልፀዋል፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘ ፓርቲው በደብረማርቆስ በሚገኘው ፅ/ቤቱ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ በአዲስ አበባ በአንድነት ፓርቲ አመራር አባላት፣ ደጋፊዎችና በሰልፉ ታዳሚዎች ላይ የደረሰውን እጅግ አሰቃቂ ድብደባ አውግዟል፡፡ የደረሰው ድብደባም ‹‹የእኛን አቅም የሚያጎለብት እንጂ የሚያንበረክክ አይደለም›› ሲሉ በመግለጫው አውስተዋል፡፡
አንድነት ፓርቲ ከዚህ ቀደም በደብረማርቆስ ከተማ የሚሊየኖች ድምፅ ንቅናቄ ወቅት የተሳካ የተቃውሞ ሰልፍ ማካሄዱ ይታወሳል፡፡

