በአዲስ አበባ በ23ቱም ወረዳዎች ቅስቀሳው በበራሪ ወረቀት ቀጥሏል፡፡ የአንድነት አባላቶች እስር ቀጥሏል!!
የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ አንድነት የ23 ወረዳዎች የአዲስ አበባ መዋቅር የበራሪ ወረቀት ቅስቀሳቸውን አጠናክረው ቀጥለዋል ፡፡የአዲስ አበባ ምክር ቤት በፓርቲው ብሔራዊ ምክር ቤት የተወሰነውን የማይቀለበስ ውሳኔ በማፅቅ አባላቱ ወደ ተግባር እንዲገቡ ባስተላለፈው መመሪያ በተጠንቀቅ የነበሩት 23ቱ ወረዳዎች በእኩል ሰዓት ቅስቀሳቸውን አጠናክረው ቀጥለዋል፡፡የአዲስ አበባ አባላት የተዘጋጀውን በራሪ ወረቀት ምክር ቤቱ ስብሰባ ከመግባቱ በፊት በየወረዳው አሰራጭተው የምክር ቤቱን ውሳኔ በትእግስት ይጠባበቁ እንደነበር እና ውሳኔው እንደተላለፈ ወደ ተግባር መግባታቸውን ለማወቅ ለችሏል፡፡ከማዕከል ይጀመራል ብለው የሚጠብቁ የደህነነት አካላት የሚይዙ የሚጨብጡትን አጥተዋል፡፡የአንድነት የትግል ስትራቴጂ ከኢህአዴግ የደህንነት መዋቅር በላይ መሆኑንም አመላክቷል፡፡
በተያያዝም ዜና ቀደም ሲል በደህንነት ሃይሎች በቅስቀሳ ላይ ሳሉ በቁጥጥር ስር የዋሉትን የብሄራዊ ምክር ቤት አባላት አቶ ያሬድ አለማሁ እና አቶ ሲሳይ ጌትነት ለመጠየቅ ባልደራስ አካባቢ ወደሚገኘው ፖሊስ ጣቢያ ያመሩት የአዲስ አበባ ምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ ለገሰ ተፋረደኝ ለእስረኞቹ እራት ለመግዛት በእቅራቢያው ወደሚገኝ ምግብ ቤት በማምራት ላይ ሳሉ ሲቢል በለበሱ ደህንነቶች አማካይነት ከዛንቺስ አካባቢ ወደሚገኘው ፖሊስ ጣቢያ መወሰዳቸው ታውቋል፡፡




