ፍ/ቤቱ በተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮች ላይ ሁለት ተለዋጭ ቀጠሮዎችን ሰጠ

ለጥር 7 እና ለጥር 26/2007 ዓ.ም ቀጠሮ ተሰጥቷል

በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር

10689483_639978259461169_7121435552203334439_nበእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ ተመስርቶባቸው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታየ የሚገኙት የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮችን ጨምሮ 10ሩም ተከሳሾች በፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ 19ኛው ወንጀል ምድብ ችሎት ሁለት ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጠባቸው፡፡

ዛሬ ታህሳስ 24 ቀን 2007 ዓ.ም ከፍተኛው ፍርድ ቤት የሰማያዊ፣ የአንድነትና የአረና ፓርቲዎች አመራሮች የሆኑት አቶ የሺዋስ አሰፋ፣ አቶ ሀብታሙ አያሌው፣ አቶ ዳንኤል ሺበሺ እና አቶ አብርሃ ደስታ እንዲሁም አንደኛ ተከሳሽ ዘላለም ወርቅአገኘሁን ጨምሮ የስድስት ተከሳሾችን ሁለት ጉዳዮች ለማየት ነበር ችሎቱ የተሰየመው፡፡

አንደኛው ጉዳይ ተከሳሾቹ በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት የሰብዓዊ መብት ጥሰት እየደረሰባቸው መሆኑን ለፍርድ ቤቱ ማስረዳታቸውን ተከትሎ ማረሚያ ቤቱ ቀርቦ እንዲያስረዳ ፍርድ ቤቱ ቀደም ብሎ የሰጠውን ትዕዛዝ በተመለከተ መልስ ለመስማት ነበር፡፡ ሁለተኛው ጉዳይ ደግሞ ተከሳሾች በጠበቆቻቸው አማካኝነት የመጀመሪያ ደረጃ የክስ መቃወሚያ አቅርበው ስለነበር በክስ መቃወሚያቸው ላይ አቃቤ ህግ የሚሰጠው የመቃወሚያ መቃወሚያ ካለ ለመስማት ነበር፡፡

በመሆኑም አንደኛው ጉዳይ ላይ ፍርድ ቤቱ አቤቱታው በቃል ተሰምቶ በመቅረጸ ድምጽ ተቀድቶ እንደገና በጽሑፍ ተገልብጦ ከመልስ ጋር እንዲቀርብ ታዝዞ የነበር ቢሆንም ድምጹ በወረቀት ተገልብጦ ስላልደረሰ ሌላ ተለዋጭ ቀጠሮ ለጥር 7 ቀን 2007 ዓ.ም ማረሚያ ቤቱ መልሱን ይዞ እንዲቀርብ ትዕዛዝ ተሰጥቷል፡፡

ሁለተኛው ጉዳይን በተመለከተ ደግሞ ፍርድ ቤቱ የአቃቤ ህግን የተከሳሾች መቃወሚያ ላይ የቀረበ መቃወሚያን ተቀብሏል፡፡ በመሆኑም በተከሳሽ መቃወሚያ ላይ የቀረበውን የፌደራል አቃቤ ህግ መቃወሚያ መርምሮ ብይን ለመስጠት ለጥር 26 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡