እንደ ሰው ወይስ እንደ እንስሳ
The Indian Folktales በተሰኝ ከዛሬ 100 ዓመት በፊት በ1919 እኤአ በታተመ መጽሐፍ ላይ እንዲህ ይላል፡፡
አንድ የሕንድ ጠቢብ ደቀ መዝሙሮቹን ሥራ እንዲሠሩ አዘዛቸውና ራቅ ብለው በከፍታ ቦታ ላይ ይመለከታቸው ጀመር፡፡ ከጥቂት ደቂቃ በኋላ ተመልሶ ደቀ መዝሙሮቹን ሰበሰባቸው፡፡ ከዚያም እንዲህ አላቸው ‹‹ከእናንተ መካከል የተወሰናችሁ እንደ ሰው የተወሰናችሁት ደግሞ እንደ እንስሳ ስትሠሩ ነበር›› ተማሪዎቹም ተገርመው ጠየቁት፡፡ መምህሩም ‹‹እንደ እንስሳ መሥራት ማለት አንድን ነገር መጎተት፣ መሸከም፣ መግፋት፣ ማዞር ወይም የሚደርስበት ቦታ ማድረስ ማለት ነው፡፡ ምን እየሠራ እንደሆነ፣ ለምን እየሠራ እንደሆነ፣ የሚመጣው ውጤት ምን እንደሆነ፣ ዓላማው ምን እንደሆነ አያስብም፡፡ በሥራው ላይም ከራሱ አስቦ አንዳች አይጨምርም፡፡ የዛሬ ሺ ዓመት አንድ ዝሆን የሠራውን ዛሬም ሌላ ዝሆን በተመሳሳይ መልኩ ይሠራዋል፡፡(አንድ ሊቅ ‹ዕብደት ማለት አንድ ውጤት እንደማያመጣ እየታወቀ በተደጋጋሚ መሥራት ነው› ብሎ ነበር) አያሻሽለውም፡፡ ምናልባት ከሰው በላይ ተሸክሞ፣ ስቦ፣ ገፍቶ፣ ቆፍሮ፣ ሮጦ፣ ደክሞ፣ ይሆናል፡፡ ያ ግን እንስሳውን ጠንካራ ያስብለዋል እንጂ ጎበዝ አያስብለውም፡፡ጉብዝና አእምሮ አለበት፡፡ እንደ እንደስሳ የሚሠሩ ሰዎች እንጂ እንደ ሰዎች የሚሠሩ እንስሳት የሉም የተባለውም ለዚህ ነው፡፡
እንደ እንስሳ የሚሠሩ ሰዎች እንደዚህ ናቸው፡፡ የተሰጣቸው ሥራ ያለ መለገም ይሠራሉ፡፡ ሲቆፍሩ፣ ሲገነቡ፣ ሲያመላልሱ፣ ሲያርሱ፣ ሲያጭዱ፣ ሲሸከሙ፣ ሲሰፉ፣ ሲፈጩ ይውላሉ፡፡ የሚሠሩት ያለ የሌለ ጉልበታቸውን ሁሉ ተጠቅመው ነው፡፡ ነገር ግን ጉልበታቸው እንጂ አእምሯቸውን አያሠሩትም፡፡ አርባ ዓመት፣ ሃምሳ ዓመት ተመሳሳይ የሆነን ሥራ ያለ ምንም ማሻሻል ሲያከናውኑ ታያላችሁ፡፡ የጻፉት ወረቀት፣ የሰፉት ልብስ፣ ያመረቱት እህል፣ የሠሩት ቤት ምን እንደሚሆን አያስቡም፡፡ እስኪ ቀየር አድርገን፣ አሻሽለን፣ ለውጠን፣ በተለየ መንድ እንሥራው አይሉም፡፡ ስለዓላማው፣ ስለሚከተለው ነገር፣ ስለሚያደርጉት ጥንቃቄ፣ ስለ ዕውቀት መሻሻል ምንም ነገር አያስቡም፡፡ እንዲያውም አእምሮ ያለው መጥቶ ለውጥ ሲያመጣባቸው ዓለም ያለፈች ይመስላቸዋል፡፡ ታላቅነታቸውን የሚያስመሰክሩት ያንን ብቻ በማድረግና ያን ጠብቆ በመኖር ነው፡፡ ለምን እንደሚያደርጉትና ለምን እንደሚጠብቁት ግን አያውቁም፡፡ብቻ ያ ነው ሥራቸው፡›› አላቸው፡፡
ተማሪዎቹም ራሳቸውን ነቀነቁ፡፡ ‹‹ከእናንተ መካከል አንዳንዶቻችሁ እንደ ሰው አንዳንዶቻችሁም እንደ እንስሳ ስትሠሩ አየኋችሁ፡፡›› አለ መምህሩ፡፡ ተማሪዎቹም ‹‹እንደ ሰው መሥራት ምንድን ነው? መለኪያውስ ምንድን ነው?›› ሲሉ ጠየቁት፡፡ መምህሩም እንዲህ አላቸው፡፡ ‹‹እንደ ሰው መሥራት ማለት ቢያንስ እነዚህን አራት ነገሮች ለማድረግ መቻል ነው፡፡
1. ሥራን ሲሠሩ የሚያስከትለው ውጤት ዐውቆ መሥራት፡- ሥራን ስትሠሩ ምን ውጤት ያመጣል? ዓላማው ምንድን ነው? የእኔ ድርሻ ምንድን ነው? የሚያስከትለው በጎና ክፉ ነገር ምን አለ? የዚህ ሥራ ትልቁ ሥዕል ምንድን ነው? ብላችሁ አስቡ፡፡ ድንጋይ ፍለጡ ስለተባላችሁ፣ ጉድጓድ ቆፍሩ ስለተባላችሁ ወይም ልብስ ሥሩ ስለተባላችሁ በቻ አትሥሩ፡፡ እናንተ የምትሠሩት ሥራ የመጨረሻው ውጤቱ ምን እንደሆነ አስባችሁ ሥሩ፡፡ ያ ከሆነ ለጥራት ትጨነቃላችሁ፤ለውበት ታስባላችሁ፤ ሀገራችሁን፣ ሕዝባችሁን እያሰባችሁ ትሠራላችሁ፡፡ ራሳችሁን የታላቅ ዓላማ አካል እንጂ የአንዲት ቁራጭ ሥራ ሠራተኛ አታደርጉትም፡፡
2. በጥንቃቄ መሥራት፡– ማንኛውም ሥራ የሚያመጣው በጎና ክፉ ነገር ይኖራል፡፡ ሰው ማለት ክፉን ነገር እየቀነሰ በጎን ነገር እያበዛ የሚሄድ ፍጡር ነው፡፡ የምትሠሩት ሥራ ጥፋት እንዳያስከትል፣ ጉዳት እንዳያመጣ፣ ሌሎችን እንዳይረብሽ፣ ሌሎች የሠሩትን እንዳያበላሽ፣ አስባችሁ ሥሩ፡፡ የእናንተን ሥራ መሥራትና የተሰጣችሁን መጨረሳችሁን ብቻ የምታዩ ከሆነ ሰዎች ሳትሆኑ እንስሳት ሆናችኋል ማለት ነው፡፡ እያሰባችሁ አይደለም ማለት ነው፤ ጡንቻችሁ እንጂ አእምሯችሁ አላደገም ማለት ነው፡፡ ለተሰጣችሁ ዕቃ፣ ለሰውነታችሁ፣ ለጤናችሁ፣ ለአካባቢያችሁ፣ ለሌሎች ሰዎች፣ ለእንስሳት፣ ለዕጽዋት፣ ጥንቃቄ አድርጉ፡፡ ስትሠሩ ምንም ዓይነት ጉዳት እንዳታስከትሉ ተጠንቀቁ፤ ጉዳት ቢመጣ እንኳን ለመቀነስ ጣሩ፡፡ ግዴለሾ አትሁኑ፡፡ ግዴለሽ ሰው ሠራተኛ አይባልም፤ አጥፊ እንጂ፡፡
3. ከሚጠበቀው በተሻለ መሥራት፡ የተሰጣችሁን ሥራ ከተሰጣችሁ በተሻለ መልኩ በመሥራት ከሚጠበቅባችሁ የበለጠ ውጤት አስመዝግቡ፡፡ ያንኑ የተሰጣችሁን ብቻ የምትሠሩ ከሆነማ ከእንስሳ ምኑን ተሻላችሁት፡፡ አንድን ዝሆን ዕቃ አሸክመን ብንልከው፤ በዝሆን ፍጥነት ተጉዞ ዕቃውን ያደርሳል እንጂ ፍጥነቱን ስለማሻሻልና በአቋራጭ መንገድ ስለ መጠቀም አያስብም፡፡ እናንተም እንዲሁ የተሰጣችሁን ብቻ የምትሠሩ ከሆነ ጠንካራ ልትሆኑ እንጂ ጎበዝ ልትሆኑ አትችሉም፡፡ ጎበዝ ማለት ስለ ተሻለ ነገር ለማሰብ የሚችል ማለት ነው፡፡
4. በዕውቀት ላይ ተመሥርቶ መሥራት፡- ሥራን ስትሠሩ ዐውቃችሁት ሥሩ፤ መለካት ካለባችሁ በመለኪያ ተጠቀሙ፤ መመዘን ካለባችሁ በመመዘኛ ተጠቀሙ፤ እናውቀዋለን፣ ለምደነዋል ብላችሁ በግምት አትሥሩ፡፡ የተሰጣችሁ መመሪያ ካለ እርሱን ተከተሉ፤ የተሰጣችሁን ዝርዝር ሥራ ተመልከቱና የጎደለ ወይም የማያስፈልግ ካለ አስተክክሉ፤ መቼ ጀምራችሁ መቼ መጨረስ እንዳለባችሁ አስቡ፡፡ ምንም የተማራችሁና ዐዋቂዎች ብትሆኑ ስለምትሠሩት ሥራ መጀመሪያ ጠይቁና ተረዱ፤ አስፈላጊ መሣሪያ ሳትይዙ አትሥሩ፡፡ እናውቀዋለን ከምትሉ ላናውቀው እንችላለን ብላችሁ ለማወቅ ሞክሩ፡፡
እንስሳ ዕውቀት የለውም፤ የሚሠራውን በዕውቀት ተመርቶ አይሠራም፡፡ ስለ ጫኑት ይጫናል፤ ስለ ጎተቱት ይሄዳል፤ ስላረሱበት ያርሳል፡፡ እናንተ ግን ጉልበታችሁን አእምሯችሁ ይምራው፡፡ ይህ ነው እንደ ሰው መሥራት ማለት፡፡››
እኛስ እንዴት እየሠራን ነው? እንደ ሰው ወይስ እንደ እንስሳ?
