በአምስት ዓመቱ ሕፃን ላይ የግብረ-ሰዶም ጥቃት የፈፀመው በ20 ዓመት እሥራት ተቀጣ Man who raped 5-year-old boy sentenced to 20 years

ሰንደቅ 10ኛ ዓመት ቁጥር 485 
በአሸናፊ ደምሴ

አስራ ሦስት ዓመት ባልሞላው ሕፃን ላይ የግብረ ሰዶም ጥቃት ፈፅሟል ሲል የፌዴራሉ ዐቃቤ ሕግ ክስ የመሠረተበት የ23 ዓመቱ ወጣት ሳሙኤል መርዕድ ጥፋተኛ ሆኖ በመገኘቱ በ20 ዓመት እሥራት እንዲቀጣ የፌዴራሉ የመጀመሪያ ፍርድ ቤት 7ኛ ወንጀል ችሎት ከትናንት በስቲያ ታህሳስ 13 ቀን 2007 ዓ.ም የቅጣት ውሳኔ አስተላለፈበት።

ዐቃቤ ሕግ ለፌዴራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት 7ኛ ወንጀል ችሎት በየካቲት 06 ቀን 2006 ዓ.ም ባቀረበው ክስ ላይ እንደዘረዘረው፤ የ23 ዓመቱ ወጣት ከእርሱ ጋር አንድ አይነት ፆታ ባለውና ዕድሜው ከ13 ዓመት በታች በሆነው ታዳጊ ልጅ ላይ የግብረ- ሰዶም ጥቃት ለማድረስ አስቦ ተንቀሳቅሷል ይላል።
በዚህም መሠረት በጥቅምት 24 ቀን 2006 ዓ.ም በግምት ከቀኑ 8፡00 ሲሆን በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ቀበሌ 01/02/03 ክልል ልዩ ቦታው ጌሾ ተራ ተብሎ ከሚጠራው አካባቢ እድሜው አምስት ዓመት በሆነው የግል ተበዳዩን ህጻን ኳስ ከሚጫወትበት ሜዳ ላይ ጠርቶ፤ ጭር ወዳለና ሰው ወደማይዘዋወርበት ቦታ በመውሰድ ሱሪውን አውልቆ የግብረ-ሰዶም ጥቃት ፈፅሞበታል ሲል ያትታል።
በዚህም ሳያበቃ ተከሳሽ የ5 ዓመቱን የግል ተበዳይ ህዳር 1 ቀን 2006 ዓ.ም ከቀኑ 6፡00 ሰዓት ሲሆን ከላይ በተጠቀሰው ቦታ ተመሳሳዩን የግብረ-ሰዶም ጥቃት በህፃኑ ላይ ሊፈፅምበት ሲሰናዳ ሰው ደርሶ ያስጣለው በመሆኑ በፈፀመው ለአካለ መጠን ባልደረሱ ልጆች ላይ የሚፈፀም የግብረ-ሰዶም ጥቃት ወንጀል ክስ ተመስርቶበታል ይላል።
የፌዴራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት 7ኛ ወንጀል ችሎትም፣ የዐቃቤ ሕግን ክስ የሰውና የሰነድ ማስረጃዎች መርምሮ ሲያበቃ፤ ተከሳሹ የተመሰረተበትን ክስ በሚገባ ሊከላከል ባለመቻሉ ታህሳስ 8 ቀን 2007 ዓ.ም ጥፋተኛነቱ ተረጋግጧል። በዚህም መሠረት የግራቀኙን የቅጣት አስተያየት ያዳመጠው ችሎቱ፤ ተከሳሽ ምንም ዓይነት የቅጣት ማቅለያ አለማቅረቡን እና ዐቃቤ ሕግ በበኩሉ ድርጊቱ በተደጋጋሚ ጊዜ የተፈፀመ ስለመሆኑ በመጥቀሱ የቅጣት ማክበጃ በማቅረቡ፤ የወንጀሉን መካከለኛ ደረጃነት በአንድ እርከን ከፍ አድርጎታል።
በመሆኑም ተከሳሹ ዕድሜው 13 ዓመት ባልሞላው እና የአምስት ዓመት ዕድሜ ባለው ህጻን ልጅ ላይ በፈፀመው የግብረ-ሰዶም ጥቃት ጥፋተኛ ሆኖ በመገኘቱ በ20 ዓመት እስራት እንዲቀጣ ሲል ችሎቱ የቅጣት ውሳኔ አስተላልፏል። 

Receive Ethiopian News and Videos by email. Sign up for Email alerts

ትኩስ እና ሰበር ዜና፣ በብዛት የታዩ ቪድዮዎችን፣ ድራማዎችን፣ሙዚቃዎችን፣ ጠቃሚ ምክሮችን እና አስገራሚ ታሪኮችን በኢሜል አድራሻዎ እንልካለን። ኢሜሎን ያስመዘግቡ።