እኛ ቀጥለናል! – ተመስገን ደሳለኝ

«የሃይለማሪያም ደሳለኝ ቁልቁለቶች» በሚል በተመስገን ደሳለኝ ከጻፈው የተወሰደ (ክፍል 4)

ግንባሩ ‹‹ባለራዕይ›› በማለት ካቆለጳጰሰው የቀድሞ ሊቀ-መንበሩ አቶ መለስ ህልፈት በኋላ፣ በጠባብ ብሔርተኞችና ጥቅመኞች በመሞላቱ መተካካቱን ተከትሎ ይፈረካከሳል የሚል ከውስጥም ከውጪም የሚሰማ ሹክሹክታ ነበር፡፡ በርግጥም የኃይለማርያም ወደ መንበሩ መምጣት ‹‹በአማራና ኦርቶዶክስ የምትመሰለው ሀገር፣ የአናሳውም ሆናለች›› ከሚለው የአቦይ ስብሐት እንቶ ፈንቶ ውጪ፣ ከተጠበቁት ሁነቶች ብዙዎቹን (በተለይ ሥርዓታዊ ልልነት ይፈጠራል የሚለው) በገቢር ከመስተዋል አልታደጋቸውም፡፡ ለዚህም ሁለት ማሳያዎችን እጠቅሳለሁ፡፡ የመጀመሪያው ባሳለፍነው ሳምንት በጠቅላይ ሚኒስትሩ በቀረበው ሪፖርትና ማብራሪያ ላይ ተደጋግሞ የተነሳው ‹‹የአፈፃፀም ችግር›› የሚለው ነው፡፡ የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ተብሎ ከበሮ ከተደሰቀለት የተቀመጠ ግብ አኳያ፣ ነባራዊው ሁኔታ ስምም አለመሆኑን ራሱ ኃይለማርያምም ‹‹የአፈፃፀም ጉድለት›› በሚል የዳቦ ስም ሊያሳብብ ከመሞከር በቀር አልካደውም፡፡ አንድ ማዕከላዊ መንግስትን የሚመራ ግንባር፣ ሊያውም እስከ ቤተሰብ የወረደ የኃይል ማዕከል ለመገንባት የሚጥር ስብስብ፤ ከተሞችን እያሰቃየ ላለው የመሰረታዊ ግልጋሎቶች ዕጦትና የተቀመጡ ዕቅዶች አለመሳካት ይህን በመከራከሪያነት ማቅረቡ፤ የስርዓቱ ተቋማት መፈረካከስን ከማስረገጥ ያለፈ የሚነግረን ምስጢር የለውም፡፡

ሌላኛው የአማካሪዎቹ ስብስብ ጉዳይ ነው፡፡ ሰውዬው ከጎኑ የሰበሰባቸውን ጉምቱ ፖለቲከኞች ትተን፤ ለእያንዳንዱ ጉዳይ ካውንስል የማቋቋም ፍጥነቱን ብናስተውል ስርዓቱ በመለስ ዘመን የነበረውን ጥብቅነት አጥቶ መዋለሉን እንረዳለን፡፡ በኢኮኖሚ ጉዳዮች ላይ እንዲመራ ካስቀመጠው ዶ/ር ደብረፅዮን ውጪ፣ ‹‹የኢኮኖሚ ካውንስል›› በሚል አይረቤ ስም ለማቋቋም መሞከሩ ሳይበቃ፤ በባጀት ዕጥረት እየተሰቃየ ያለውን አስተዳደሩን ለመታደግ የፋይናንሻል ምንጮችን ከውጪ የሚያፈላልግ ሌላ ካውንስል መሰል ስብስብ ማደራጀቱን ስንታዘብ፤ ስርዓቱ ቢያንስ እንደ መለስ ዘመን መቀጠል በማያስችል ወላዋይነት /Brittle state/ ለመፈተኑ ጥቁምት ይሰጠናል ብዬ አስባለሁ፡፡ በተለይም ጠቅላይ ሚንስትሩ በሪፖርቱ ላይ የአገሪቱን የውጭ ምንዛሪ ፍላጎት ለማሟላት መንግስት የሐዋላ አግልግሎትን ማጠናከር እንዳለበት ከመግለፅ ባለፈ፣ ከ2000 ዓ.ም መጀመሪያ አንስቶ የህንዱን ካራቱሪ እና ሳውዲ ስታርን ጨምሮ ለበርካታ ባለሀብቶች ስለተሰጠው ሰፋፊ የእርሻ መሬት አንዳችም ነገር ትንፍሽ አለማለቱ የክስረቱ ዋነኛ ማሳያ ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም በወቅቱ ከመሬት ቅርምት ጋር አያይዘው የተቃውሞ ድምፃቸውን ላሰሙ ምሁራንም ሆነ ‹‹አንድ ሄክታር መሬት በሃያ ብር›› መሰጠቱን በመኮነን የድርጊቱን ኢ-ፍትሓዊነት በዘገባው ለገለፀው ታዋቂው ‹‹ኒዎርክ ታይምስ›› ጋዜጣ፣ መለስና ጓዶቹ መከራከሪያ አድርገው ያቀረቡት ‹‹በአጭር ጊዜ ውስጥ የውጭ ምንዛሬ ችግራችንን ይቀርፋል፣ የቴክኖሎጂና የሙያ ሽግግር እንዲደረግ ያስችላል›› የሚል እንደነበረ አይዘነጋም፡፡ ግና፣ ዛሬ ይህ ጉዳይ ሕልም ሆኖ ለውጭ ምንዛሪ ሐዋላን የሙጥኝ መባሉን እየሰማን ነው፡፡ እንዲሁም በራሱ በመለስ ዜናዊ በ2005 ዓ.ም በርግጠኝነት መውጣት እንደሚጀመር የተነገረለት የነዳጅ ክምችትም ቢሆን፣ ‹‹ውሾን ያነሳ…›› እንዲሉ የተዘጋ ፋይል ሆኗል (በነገራችን ላይ በፓርላማው. የፓርቲው ካድሬዎች ባለስልጣናቱ ላይ የሚያዘንቡት የጥያቄ እሩምታ የሚያመለክተው፣ ፓርላሜንታዊ ዴሞክራሲ ዘግይቶ ወደ ኢህአዴግ ሰፈር መምጣቱን ሳይሆን፣ የፓርቲውን የውስጥ የዕዝ ተዋረድ መሰነጣጠቁን እና ቡድንተኛነት ግንባሩን እያመሰው መሆኑን ነው፡፡ በተቀረ ከዚህ ውጪ ያለው መከራከሪያ ሁሉ ጥሩ የአደባባይ ቧልት ከመሆን የሚያልፍ አይመስለኝም) የሆነው ሆኖ ከላይ ኃይለማርያምን ያብራሩልናል ብዬ ለመጥቀስ ከሞከርኳቸው ጭብጦች በእጅጉ ባለፈ፣ ሪፖርቱን ያቀረበበት ተአብዮ እና የማንአለብኝነት መንፈስ በቅድመ-ምርጫው አንድ ዓመት ውስጥ አንዳችም የፖለቲካ ማሻሻያ እንዳትጠብቁ የሚለው ዋነኛው ሲሆን፤ አቦ ሌንጮ ለታ ‹‹ሰዎች አሳስተውታል›› እንዳለው፤ ዙሪያው ያሉት አለቆች እንዳዘዙት፤ ‹እኛ እየረገጥናችሁ እንቀጥላለን፣ እናንተም በተጨቋኝነታችሁ አዝግሙ› የሚለው ደግሞ ሌላኛው ውስጠ-ወይራ ጥብቅ መልእክቱ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡

በመጨረሻም ጠቅላይ ሚንስትር ኃ/ማርያም ጥር 2003 ዓ.ም. ‹‹ምዕራፍ›› ከተሰኘ ኃይማኖታዊ መጽሔት ጋር ቃለ-መጠይቅ ባደረገበት ወቅት ‹‹ከመጽሐፍ ቅዱስ ደስ የሚልዎት ቃል የቱ ነው?›› በሚል ለቀረበለት ጥያቄ የሰጠውን ምላሽ፣ አንድም ዛሬ የሚከተለውን መንገድ ቆም ብሎ እንዲፈትሽ ለማስታወስ፤ ሁለትም ለዚህ ተጠይቅ መደምደሚያ ይሆን ዘንድ ወደጃለሁና እንደሚከተለው አሰፍረዋለሁ፡-