ቤተ ክርስቲያኒቱ ‹‹ኦዲት አንደረግም›› ላሉ ግለሰቦች ሽፋን የሰጡ የመንግሥት ባለሥልጣናትን ተቃወመች
- ‹‹ግለሰቦቹ ጉዳዩን ፖለቲካዊ በማድረግ ከተጠያቂነት ለማምለጥ እየተሯሯጡ ነው›› /የደብሩ አስተዳደር/
- ላልተጠናቀቀው ቤተ ክርስቲያን ሕንፃ ወጪ የተደረገው 8 ሚሊዮን ብር የተጋነነ ነው ተብሏል
(ኢትዮ – ምኅዳር፤ ቅጽ፪ ቁጥር ፷፮፤ ረቡዕ ሚያዝያ ፳፱ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም.)
በሚሊዮን የሚቆጠር የምእመናን ገንዘብ ለብክነትና ዘረፋ እንደተዳረገበት የተጠቆመው የድሬዳዋ ቅዱስ ገብርኤል ደብር ቤተ ክርስቲያን ሕንፃ ግንባታና ሒሳብ እንዲመረመር ከቅዱስ ሲኖዶስ የተላለፈውን መመሪያ ባለመቀበልና ጉዳዩን ‹‹ፖለቲካዊ ልባስ በመስጠት ከተጠያቂነት ለማምለጥ›› ከፍተኛ ሩጫ ላይ መኾኑ ለተገለጸው የሕንፃ አሠሪ ኮሚቴ ሽፋን ይሰጣሉ ያላቸው የከተማው የመንግሥት ተቋማት ሓላፊዎች እጃቸውን ከማስገባት እንዲቆጠቡ ጥብቅ መመሪያ እንዲሰጥለት የደብሩ አስተዳደር የከተማውን ከንቲባ ጽ/ቤት ጠየቀ፡፡
ባለፈው ሳምንት ረቡዕ ለከንቲባው ጽ/ቤት የተጻፈው የደብሩ ደብዳቤ÷ የሕንፃ ግንባታው ጥራት በገለልተኛ የመንግሥት ሥራና ከተማ ልማት ባለሞያዎች፣ ገቢና ወጪ ደግሞ በብቁ የሒሳብ ባለሞያዎች እንዲመረመር ቅዱስ ሲኖዶስ መስከረም 8 ቀን 2006 ዓ.ም. ለሀገረ ስብከቱ ያስተላለፈውን መመሪያ አስታውሶ፤ ይህንኑ ውሳኔ ተግባራዊ ለማድረግ የሕንፃ አሠሪ ኮሚቴው ሒሳቡን እንዲያስመረምር በደብሩ አስተዳደር በተደጋጋሚ ቢጻፍለትም መመሪያውን ‹‹ኢ-ሕጋዊ በማስመሰልና ለመንግሥት ተቋማት የማሳሳቻ አቤቱታ በማቅረብ›› ለመታዘዝ ፈቃደኛ አለመኾኑን ደብዳቤው ገልጦአል፤ ‹‹እንቅስቃሴው አቅጣጫውን እንዳይስትና ከመሥመር እንዳይወጣም›› ቢሮውን በማሸግ ኮሚቴውን እንዳገደውም አስታውቋል፡፡
የታሸገው የሕንፃ አሠሪ ኮሚቴ ቢሮ የፖሊስ አባላት፣ ካህናት፣ የሰንበት ት/ቤት፣ የስብከተ ወንጌልና የምእመናን ተወካዮች በታዛቢነት በተገኙበት ሚያዝያ 21 ቀን 2006 ዓ.ም. ተከፍቶ፤ የንብረትና ሰነድ ቆጠራ በመደረግ ላይ ሳለ ቀጣና 02 ከተባለ ፖሊስ ጣቢያ የተመደቡት ኹለት ፖሊሶች በጣቢያው ትእዛዝ የታዛቢነት ሥራቸውን ትተው እንዲመለሱ መደረጉን ደብዳቤው አስረድቷል፡፡ ኹኔታው በምእመናኑ ዘንድ ‹‹ፖሊስ የሕዝብ ነው ወይስ የግል?›› የሚል ጥያቄ ማስነሣቱን የጠቀሰው የደብሩ አስተዳደር፣ በታዛቢነት ሥራ ላይ የነበሩ ፖሊሶች በጣቢያው ሓላፊ እንዲመለሱ መታዘዛቸው ‹‹ቤተ ክርስቲያኒቱን ወንጀለኛ ለማድረግና የግለሰቦችን ፍላጎት ለማሟላት›› የታለመ ነው ብሎታል፡፡
በንብረትና ሰነድ ቆጠራው በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ያልተመዘገቡ ሕገ ወጥ ደረሰኞችና ማኅተም እንዲሁም ለሥራ ማስኬጃ ከተፈቀደው በላይ የኾነና በባንክ መቀመጥ የሚገባው ብር 57,000 ጥሬ ገንዘብ የተገኘ ሲኾን፣ የፖሊሶቹን ወደ ጣቢያ መመለስ ተከትሎ ሒደቱን ለማስቆምና የሒሳብ ምርመራውን ለማስተጓጎል በደብሩ አስተዳዳሪና በሰበካ ጉባኤው ምክትል ሊቀ መንበር ላይ በአንዳንድ የመንግሥት ሓላፊዎች ቀጥተኛ ጫና እየተደረገ እንዳለ ደብዳቤው አስታውቋል፡፡ ጫናው ‹‹የሕዝብን ገንዘብ ተቀብለው ሒሳብ አናስመረምርም ላሉ ግለሰቦች ሽፋን መስጠት›› መኾኑን በማተት፣ ለሕገ ቤተ ክርስቲያን የማይገዛና ግልጽነት የሚጎድለው አሠራር ሊጠየቅ እንደሚገባው አመልክቷል፡፡
‹‹ኦዲት አንደረግም›› ለሚሉ ግለሰቦች ‹‹አዎ፣ አይመርመሩ›› የሚል ሽፋን የመስጠት አካሔድ የቅዱስ ሲኖዶሱን መመሪያ የሚጥስ፣ ቤተ ክርስቲያኒቱንና መንግሥትን የሚያጣላ ጣልቃ ገብነት ከመኾኑም በላይ የቤተ ክርስቲያኒቱን መብትና ጥቅም የሚያስቀር መኾኑን የደብሩ አስተዳደር አሳስቧል፤ የሕዝብ ገንዘብን በማባከን ከተጠረጠሩት የሕንፃ አሠሪ ኮሚቴው አባላት ጋር ቅርበት ያላቸው የከተማው የመንግሥት ባለሥልጣናት እጃቸውን ከማስገባትና ተጽዕኖ ከመፍጠር ይቆጠቡ ዘንድ ጥብቅ መመሪያ እንዲሰጥለትም የከንቲባውን ጽ/ቤት ጠይቋል፡፡
በደብሩ ጽ/ቤት የተጠቀሰው አቤቱታ በቀጥታ ይመለከታቸዋል ከተባሉትና ደብዳቤው በግልባጭ ከደረሳቸው የመንግሥት ተቋማት ሓላፊዎች መካከል የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር እንደሚገኙበት የደብሩ ምንጮች ለኢትዮ – ምኅዳር የገለጹ ሲኾን ኮሚሽነሩ በጉዳዩ ላይ ከሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ጋር እንደሚነጋገሩበት ተመልክቷል፡፡
የሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑ ሥራ ሳጠናቀቅ ሒሳቡንና ግንባታውን አላስመረምርም ማለቱ የተገለጸው የሕንፃ አሠሪ ኮሚቴው በበኩሉ በደብሩ፣ በአስተዳዳሪውና በሰበካ ጉባኤው ምክትል ሊቀ መንበር ላይ ክሥ መመሥረቱ ታውቋል፡፡ በደብሩ አስተዳደር ርምጃ በታሸገው ቢሮው በሰነድና በጥሬ በአጠቃላይ ከ26 ሚሊዮን ብር እንዳለው ያሰፈረው ኮሚቴው፣ በድሬዳዋ የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት እና በፖሊስ ጣቢያ የመሠረተው ክሥ የስም ማጥፋት ወንጀልንና ሁከት ይወገድልኝ የሚመለከት እንደኾነ ተገልጦአል፡፡
በቤተ ክርስቲያኒቱ የቃለ ዐዋዲ ድንጋጌ መሠረት የሕንፃ አሠሪ ኮሚቴው የተዋቀረው ደብሩን በበላይነት በሚያስተዳድረው ሰበካ ጉባኤ መኾኑን በመጥቀስ ኮሚቴው ለሰበካ ጉባኤው መታዘዝና የሚሰጠውንም መመሪያ ተቀብሎ ተፈጻሚ ማድረግ እንደሚጠበቅበት ያስረዱት አስተያየት ሰጭዎች፣ የሕዝብ ገንዘብ የደረሰበት ሳይታወቅ ተሸፋፍኖ እንዲቀር በፖለቲካ ሽፋንና ግለሰባዊ ትስስሮች የሚደረገው ጫና ሊቆምና የእምነት ተቋማት በራሳቸው አስተዳደራዊ መዋቅር፣ የግልጽነትና ተጠያቂነት መርሕን የማስፈን ጥረታቸው ሊበረታታ እንደሚገባው አሳስበዋል፡፡
‹‹በምሥራቅ ኢትዮጵያ ተወዳዳሪ የሌለው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን መገንባት›› በሚል በጥቅምት ወር 1998 ዓ.ም. ሥራው የተጀመረው የድሬዳዋ ሳባ ደ/ኃይል ቅ/ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በወቅቱ ለማጠናቀቅ የታቀደው በኹለት ዓመትና በሦስት ሚሊዮን ብር ወጪ ነበር፡፡ ይኹንና በውለታ ከተያዘው ጊዜ በስድስት ዓመት ዘግይቶ እስከ አኹን ከስምንት ሚልዮን ብር በላይ ለሚገመት ከፍተኛ ወጪ ከመዳረጉም ባሻገር ከዲዛይኑ ውጭ ነው የተባለው የግንባታው ጥራትም የከተማውን አገልጋዮችና ካህናት እያነጋገረ እንደሚገኝ መዘገቡ ይታወሳል፡፡
የድሬዳዋ ሳባ ደ/ኃ/ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ለቅ/ሲኖዶሱ መመሪያ ፖሊቲካዊ ትርጉም በመስጠት ኦዲት አንደረግም ላሉት የደብሩ የሕንፃ አሠሪ ኮሚቴ አባላት ሽፋን የሰጡ የከተማ አስተዳደር ባለሥልጣናትን በመቃወም ከጣልቃ ገብነት እንዲቆጠቡ ለመጠየቅ ለከንቲባው ጽ/ቤት የጻፈው ደብዳቤ


