ሲቪል ድርጅቶች – ግርማ ሞገስ

ዴሞክራሲ ስርዓት በመገምባት ላይ በሚገኙ ወይንም የዴሞክራሲ በዳበረባቸው አገሮች ውስጥ እጅግ ብዙ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች እና ተቋሞች ከመንግስት ነጻ ሆነው ይመሰረታሉ። በነፃነት ይንቀሳቀሳሉ። የጋዜጠኞች ማህበሮች፣ የጋዜጠኞች መድረኮች፣ የሰራተኛ ማህበሮች፣ የተማሪ ማህበሮች፣ የሰብዓዊ መብት ድርጅቶች፣ የስነጽሑፍ ማህበሮች፣ የኢኮኖሚ እና ማህበራዊ አሳብ አቀንቃኝ ድርጅቶች፣ የፖለቲካ አሳብ አቀንቃኝ ቡድኖች፣ የህዝብ ጤንነት እና ኑሮ ሁኔታ መሻሻል ተቆርቋሪ ድርጅቶች፣ የመንግስት ግልጽነት ታዛቢ እና አጋላጭ ድርጅቶች እና የመሳሰሉትን ድርጅቶች ማለታችን ነው።

በአንድ አገር የዴሞክራሲ ስርዓት በሃቅ ግንባታ ላይ መሆኑ ወይንም የዴሞክራሲ ስርዓት መዳበሩ የሚለካው እንደነዚህ አይነት በርካታ ድርጅቶችን ዜጎች በነፃ ማቋቋም እና በነፃነት ማንቀሳቀስ መቻላቸው ሲረጋገጥ ነው። የዴሞክራሲ ስርዓት በሚገነባባቸው ወይንም ባደገባቸው አገሮች ውስጥ በስልጣን ላይ ያለው መንግስት በህዝብ የተመረጠ ቢሆንም ህዝቡ የመረጠውን መንግስት የሚቆጣጠረው በእነዚህ ነፃ ድርጅቶቹ ተጠቅሞ ነው። እነዚህ ድርጅቶች በነፃነት መቋቋም እና መንቀሳቀስ ካልቻሉ ዜጎች መንግስታቸውን የሚቆጣጠሩበት መሳሪያ እንዳይኖራቸው ተደርገዋል ማለት ነው። ይህ ደግሞ የሚደረገው አምባገነኖች በሚያስተዳድሩዋቸው አገሮች ብቻ ነው።

ስለዚህ አንድ አገር ወደ ዴሞክራሲ ሽግግር በማድረግ ላይ መሆኗ ወይንም አለመሆኗ አንደኛው መለኪያም እነዚህ ድርጅቶች ከገዢው ፓርቲ ቁጥጥር ስር ነፃ ሆነው እንደ ልብ ማበብ እና በነፃነት መንቀሳቀስ መቻላቸው ነው።

እነዚህ ድርጅቶች ነፃ ከሆኑ የዲሞክራሲ ኃይል ምንጮች በመሆን ለዴሞክራሲ ሽግግር ከፍተኛ ግልጋሎት ይሰጣሉ። ገዢው ፓርቲ የፖለቲካ ጭፍራዎቹን በእነዚህ ድርጅቶች ላይ በመላክ ለማዳከም ከሞከር ወይንም አመራራቸው ላይ በማስቀመጥ እነዚህን ድርጅቶች በቁጥጥር ስር ካደረገ ግን ድርጅቶቹ ወደ መንግስታዊ ተቋምነት ተቀይረዋል ማለት ነው። ገዢው ፓርቲ የተለያዩ ድንጋጌዎች በማወጅ እነዚህ ድርጅቶች እንዲጠፉ ወይንም እንዲዳከሙ ካደረገም መንግስት ሆን ብሎ ወደ ዴሞክራሲ በሚደረገው ሽግግር ላይ ጦርነት ከፍቷል ማለት ነው።

ይህን የሚያደርግ መንግስት አምባገነን መንግስት እንጂ በምንም አይነት አለም አቀፍ መስፍርት ዴሞክራሲያዊ መንግስት ሊሆን አይችልም። አምባገነን አይደለሁም የሚል ከሆነ ከእነዚህ ተግባሮች መቆጠብ አለበት።