የቁጥር ጨዋታ?!
ጽዮን ግርማ
ሕፃን እዮሲያስ የጓደኛዬ ልጅ ነው። በሰባት ዓመቱ ሁለተኛ ክፍል ገብቷል። ፈጣንና መጠየቅ የሚወድ ታዳጊ ነው። ባገኘኝ ቁጥር በጥያቄ ልቤን ጥፍት ያደርገዋል። አብዛኛው ጥያቄዎቹ ትምሕርት ቤት ከጓደኞቹ ጋራ ከሚያደርጋቸው ጨዋታዎች የሚመነጩ ናቸው። ባለፈው ሰሞን እንዲህ ብሎ በእንቆቅልሽ መልክ ጠየቀኝ። ለእኔም አጠያየቁ ልጅነቴን ስላስታወሰኝ በትዝታ ፈገግታ ታጅቤ “ምናውቅልህ” አልኩት። ”እ … ቢሄዱ፣ ቢሄዱ የማይሰለቻቸው?” አለኝ። ጥያቄውን እኔ ከለመድኩት የልጅነት የእንቆቅልሽ መልስ ጋራ ለማዛመድ የዱር አልቀረኝ የቤት መንገድ አይሰለቻቸውም ስል ያሰብኳቸውን እንስሳት ማሰላሰል ቀጠልኩ። የመሰሉኝንም ስማቸውን ደረደርኩለት፤ አልተሳካልኝም።