የመረረው አብዮተኛ
በአብዮቱ ዘመን አንድ ጓድ ከዚህ ቀጥሎ የተጠቀሰውን ቃለ መጠይቅ በመስጠቱ ለ17 ዓመታት ወኅኒ ተወርውሮ ነበር፡፡ በ1983 ዓም ከወኅኒ ሲወጣ ሰውዬው አርጅቷል፡፡ ከዘራውን ተደግፎ ቤቱ በረንዳ ላይ ይቀመጥና ቃለ መጠይቁ የታተመበትን ጋዜጣ እያየ ‹‹ይህን ቃለ መጠይቅ የሰጠሁት ዛሬ ቢሆን ኖሮስ?›› ብሎ ይጠይቃል፡፡ ለሰውዬው መልስ ለመስጠት ቃለ መጠይቁን አንብቡት፡፡
ጋዜጠኛ፡- ለእርስዎ ሀብት ክፍፍልን በተመለከተ በካፒታሊዝምና በሶሻሊዝም መካከል ያለው ልዩነት ምንድን ነው?
ጓድ፡- በካፒታሊዝም እኩል ያልሆነ የሀብት ክፍፍል ሲኖር፣ በሶሻሊዝም ደግሞ እኩል የሆነ የድኽነት ክፍፍል አለ
ጋዜጠኛ፡- ጭቆናን በተመለከተ በካፒታሊዝምና በሶሻሊዝም መካከል ልዩነቱ ምንድንነው?
ጓድ፡- በካፒታሊዝም ሰው ሰውን ይጨቁናል፣ በሶሻሊዝም ግን ፓርቲ ሰውን ይጨቁናል
ጋዜጠኛ፡- ለምሳሌ በሰሐራ በረሃ ውስጥ ሶሻሊስት ሪፐብሊክ ቢመሠረት ምን ለውጥ ሊያመጣ ይችላል ብለው ያስባሉ?
ጓድ፡- ከሦስት ዓመታት በኋላ ሀገሪቱ አሸዋ ከውጭ ማስመጣት ትጀምራለች
ጋዜጠኛ፡- በሶሻሊዝም አስተሳሰብ ደመወዝና ሠራተኛን እንዴት ይገልጧቸዋል?
ጓድ፡- በሶሻሊዝም ሠራተኛም በሚገባ የሠራ ለመምሰል ጥረት ያደርጋል፣ መንግሥትም ተገቢውን ደመወዝ የከፈለ ለመምሰል ጥረት ያደርጋል
ጋዜጠኛ፡- ገበያ የሚመራው በአቅርቦትና ፍላጎት ነው ይባላል፡፡ ይህንን ሃሳብ በሶሻሊዝም እንዴት ይገልጡታል?
ጓድ፡- በሶሻሊዝም የፈለግከውን ነገር መርጠህ አትገዛም፤ ነገር ግን የቀረበልህን ነገር ትገዛና፣ ከገዛህ በኋላ እንድትፈልገው ይደረጋል፡፡
ጋዜጠኛ፡- አንዳንድ ሰዎች የሶሻሊስት ፓርቲው ጋዜጣ በጣም ትልቅ ነው ይላሉ፤ ለምንድን ነው ትልቅ የሆነው?
ጓድ፡- ምክንያቱም ሰው እርሱን መያዝ ስለሚያፍር፣ የጋዜጣው ስፋት ስታነበው ፊትህን ለመሸፈን የሚበቃ መሆን አለበት
ጋዜጠኛ፡- በዓለም ላይ ሰባቱ አስደናቂ ነገሮች የሚባሉ አሉ፡፡ በሶሻሊዝም አስተሳሰብ ሰባቱ የዓለም አስደናቂ ነገሮች ምን ምን ናቸው ብለው ያስባሉ?
1. ሁሉም ሰው ሥራ አግኝቷል
2. ሁሉም ሰው ሥራ ቢያገኝም ቅሉ ማንም ሰው ግን ሥራ እየሠራ አይደለም(ስብሰባ፣ ግምገማ፣ የፓርቲ ሥራ፣ የአካባቢ ልማት ማኅበር ሥራ አለበት)
3. ማንም ሰው ሥራ እየሠራ ባይሆንም እንኳን ሁሉም ሰው ግን ሀገሪቱ ያወጣችውን የዕድገት ዕቅድ ግቡን እንዲመታ አድርጓል
4. ምንም እንኳን ሁሉም ሰው ዕቅዱን ተግባራዊ ቢያደርገው፣ ነገር ግን ምንም ዓይነት ውጤት አልተገኘም
5. ምንም እንኳን ምንም ዓይነት ውጤት ባይገኝ፣ ነገር ግን ሁሉም ሰው የፈለገው ነገር ሁሉ እንዲኖረው ተደርጓል
6. ምንም እንኳን ሁሉም ሰው የፈለገው ነገር ሁሉ ቢኖረው፣ ሁሉም ሰው ግን በሆነው ነገር ርካታ የለውም
7. ምንም እንኳን ሁሉም ሰው በሆነው ነገር ሁሉ ርካታ ባይኖረው፣ ፓርቲው ግን የሕዝቡን 100%ድጋፍ አለው፡፡
እነዚህ ናቸው ሰባቱ አስደና ቂነገሮች፡፡
ጋዜጠኛ፡- ፓርቲው የሚመራባቸው ሦስቱ መሠረታውያን ሕግጋት ምንድን ናቸው?
ጓድ፡- ሶሻሊዝም ሩጫ ነው፤ በዚህ ሩጫ ውስጥ የፓርቲው መርሖዎች ሦስት ናቸው፡፡ የመጀመሪያው ሩጫው እንደተጀመረ ሯጮቹን ሁሉ ማሰናከልና የመሪነቱን ቦታ መያዝ ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ የሩጫውን ፍጥነት መቆጣጠር መቻል ነው፡፡ የመጨረሻውም በተቻለ መጠን ሩጫውን ሳያጠናቅቁ የመሮጫው ትራክ ላይ ረዥም ጊዜ ለመቆየት መቻልነው፡፡
ጋዜጠኛ፡- አንድ የእርስዎ ጓድ በአብዮታዊው ጦር ተይዘው በቀደም ወደ ወኅኒ ቤት ገብተዋል፡፡ ምን ጎድሎባቸው ነው ፀረ አብዮት የሆኑት፤ አብዮቱ ሁሉን ነገር አሟልቶላቸው ነበር?
ጓድ፡- ጓዱን የያዙት ሰዎችም ይህንን ነበር የጠየቁት፡፡ እርሱ ወደ አሜሪካ ለመሄድ በዝግጅት ላይ ነበር፡፡ ዝግጅቱን ሲያጠናቅቅ የመውጫ ቪዛ እንዲሰጠው አመለከተ፡፡ ይህንን የሰሙ ወታደሮች ከሌሊቱ በስምንት ሰዓት ወደ ቤቱ መጡ፡፡ በሩን ሰብረው ገቡና ‹‹አብዮቱ ቤት ሰጥቶሃል፣ መኪና ሰጥቶሃል፣ መሬት ሰጥቶሃል፣ የንግድ ድርጅት ሰጥቶሃል፣ሥልጣን ሰጥቶሃል፣ ከውጭ ዕቃ ያለ ቀረጥ እንድታስገባ ዕድል ሰጥቶሃል፤ ለምንድን ነው ወደ አሜሪካ መሄድ የፈለግከው›› ሲሉ ጠየቁት፡፡ እርሱም ተናድዶ ‹‹እንዲህ ከሌሊቱ በ8 ሰዓት እኔ ሳልፈቅድላችሁ በሬን ሰብራችሁ በመግባት እንዳትረብሹኝ ስለምፈልግ ነው አገር ጥዬ የምሄደው›› ብሎ መለሰላቸው፡፡ ለዚህ ነው ያሠሩት፡፡
ጋዜጠኛ፡- የእርስዎ ጓድ ብቻ ሳይሆኑ የጎረቤትዎ ልጅም መታሠሩን ሰምተናል፤ ልጁ በጣም ትንሽ ልጅ ነው፡፡ ደግሞም በጣም የታወቀ ዋናተኛ ነው፡፡ የታሠረውም ባለፈው ግዮን ሆቴል ዋና ተለማምዶ ሲመለስ ነው ይባላል፡፡ ምክንያቱን ሊነግሩን ይችላሉ?
ጓድ፡- እንደ ሰማሁት ከሆነ ልጁ የታወቀ ዋናተኛ ነው፡፡ አባቱ በሌለው ገንዘብ ከፍሎለት ግዮን ሆቴል ዋና ይለማመዳል፡፡ የፓርቲያችን ሊቀ መንበር በዚያ ቀን ዋና ለመዋኘት ግዮን ሄደው ነበር፡፡ በአጋጣሚ ዋና እየተለማመዱ ሳለ ወደ መካከል ሄደው ሊሰምጡ ደረሱ፡፡ አጃቢዎቻቸው ዋና የሚችሉ አልነበሩም፡፡ ልጆች ናቸው ተብለው በአካባቢው እንዲንቀሳቀሱ የተፈቀደላቸው የታሠረው ልጅና ሁለት ጓደኞቹ ብቻ ነበሩ፡፡ ሮጠው ገቡና ሊቀ መንበሩን ከመስመጥ አዳኗቸው፡፡ ጓድ ሊቀ መንበርም ለዚህ ውለታቸው አንዳች ሽልማት ሊሰጧቸው ፈለጉና ልጆቹን ጠየቋቸው፡፡ አንደኛው ልጅ ብስክሌት መረጠ፤ ሁለተኛው ልጅ ደግሞ የመጨዋቻ መኪና ጠየቀ፤ ይኼ የጎረቤቴ ልጅ ግን የአካል ጉዳተኞች መሄጃ ጋሪ መረጠ፡፡ ጓድ ሊቀ መንበርም በጣም ተገረሙና ‹‹ምን ያደርግልሃል፤ አንተ ሙሉ ጤነኛ ነህ›› አሉት፡፡ ልጁም ‹‹አባቴ እርስዎን ከሞት ማዳኔን ከሰማ እግሬን ይሰባብረዋል፤ ለዚያ ብዬ ነው›› አላቸው፡፡ በዚህ ተናደው ነው ያሳሠሩት፡፡
ጋዜጠኛ፡- ባለፈው ሰሞን ለሥራ ጉብኝት ወደ ቻይና ተጉዘው ነበር፡፡ በዚያ ጊዜ በአንድ ቻይናዊ፣ ኢትዮጵያዊና ዴንማርካዊ የፓርቲ ሰዎች መካከል የተፈጠረ ነገር እንደነበር ሰምተናል፡፡ ሊነግሩን ይችላሉ?
ጓድ፡- አዎ፤ አራታችን በአንድ ወንዝ ዳር ቆመን ስንዝናና አንድ ጋዜጠኛ መጣና ‹‹ሥጋ ለማግኘት ሲባል ሰልፍ ስለመያዝ ምን ታስባላችሁ?›› ሲል ጠየቀን፡፡ ዴንማርካዊው ‹‹ሰልፍ ማለት ምንድን ነው?›› ሲል መልሶ ጠየቀ፤ ቻይናዊውም ቀጠል አደረገና ‹‹ሥጋ ምንድን ነው?›› ሲል አከለበት፡፡ የኛው ፖለቲከኛ ደግሞ ‹‹ማሰብ ማለት ምንድን ነው?›› ብለው ጋዜጠኛውን መልሰው ጠየቁት፡፡ ይኼ ነው ታሪኩ፡፡
ጋዜጠኛ፡- በዚሁ አጋጣሚ አብዮታዊ መሪያችን በቻይና ለነበሩ ጋዜጠኞች የሃሳብ ነጻነትን አስመልክቶ አስደናቂ ነገር ተናግረዋል ይባላል፤ ምን ነበር?
ጓድ፡- ጋዜጠኛው የሃሳብ ነጻነት እያሉ ምዕራባውያን ሶሻሊስት ሀገሮችን ለመበጥበጥ ይሞክራሉ፤ እናንተ ይህንን ችግር እንዴት ፈታችሁት? ብሎ ጠየቃቸው፡፡ እርሳቸውም ‹እኛ መጀመሪያውኑ ሃሳቡ እንዳይኖር ስላደረግነው ነጻነት መስጠት አይጠበቅብንም› ብለው መልሰውለት በጣም ተደንቆ ነበር፡፡ ?
ጋዜጠኛ፡ – እኛ ራሳችን ስሕተታችንን ገምግመን ማሻሻል ባለመቻላችን ሌሎች ስሕተቶቻችንን ዐውቀው እየተጠቀሙበት ነው የሚል ትችት ሰንዝረው ነበር፡፡ አንድ ማሳያ እንኳን ሊነግሩንይችላሉ፡፡
መልስ፡- ይህንን ድክመት እንኳን ነጻ ሆኖ የሚከታተለን ሕዝብ ይቅርና ፀረ አብዮት ናቸው ብለን ያሠርናቸው እንኳን በሚገባ ዐውቀውታል፡፡ አንድ ቀላል አስቂኝ ነገር ልንገርሽ፡፡ አንድ ባልዋ ፀረ አብዮት ሆኖ የታሠረባት ሴትዮ አለች፡፡ ሴትዮዋ ድኽነቱ ሲመራት በቤቷ ጓሮ ድንች ተክላ መሸጥ ፈለገች፡፡ ግን ጉልበት ከየት ይምጣ፡፡ ሰው እንዳትቀጥር፣ ገንዘብ ከየት ይገኝ፡፡ በመጨረሻ ለባልዋ እንዲህ የሚል ደብዳቤ ጽፋ በወኅኒ ቤቱ በኩል ላከችለት ‹‹በጓሯችን ድንች ልተክል ነበር፡፡ ነገር ግን ማን ይቆፍርልኛል፤ አንተ እንዳታግዘኝም ገና ሁለት ዓመት ይቀርሃል›› ባልዋም ‹‹ጓሮውን ስትቆፍሪ ተጠንቀቂ፤ እጅግ ውድ የሆኑ ነገሮችን ደብቄበታለሁ›› ብሎ መልሶ ላከላት፡፡ ደብዳቤው በደረሳት ሌሊት ፖሊሶች መጥተው የተደበቀውን ነገር ፍለጋ የቤቷን ጓሮ ከጥግ እስከ ጥግ ቆፋፈሩት፡፡ እርሷም በድንጋጤ ከረመችና ‹‹ስድስት ፖሊሶች መጥተው የሆነ ነገር ፍለጋ ጓሮውን በቁፋሮ እንዳልነበረ አደረጉት፤ ያልቆፈሩት መሬት የለም፤ ምን ባደርግ ይሻለኛል?›› ስትል ጻፈችለት፡፡ ባሏም ‹‹አሁንማ ቆፍረውልሻል ድንችሽን ትከይ›› ብሎ መለሰላት፡፡
ጥያቄ፡- ይኼ የመጨረሻ ጥያቄያችን ነው፡፡ ባለፈው ጊዜ በአውሮፕላን ሲጓዙ አንድ ያልታወቀ ፍጡር አውሮፕላኑን እየተከተለ አስቸግሮ ነበር ይባላል፡፡ ፓይለቱና አስተናጋጆቹ ሊያባርሩት አልቻሉም፡፡ በአውሮፕላኑ የነበሩት የሃይማኖት አባቶችም ከዐቅማቸው በላይ ሆኖ ነበር፡፡ እርስዎ ግን የሆነ ነገር ሲያሳዩት እንደ ጢስ በኖ እንደ ጉም ተኖ ጠፋ ይባላል፡፡ ምን እንዳሳዩት ሊነግሩን ይችላሉ?
መልስ፡- እነርሱ ይህንን ያህል ገንዘብ እንሰጥሃለን አሉት፤ አልሄደም፤ የሃይማኖት አባቶችንም አልፈራም፡፡ ወደ እኔ ቀረብ ሲል ‹‹የወጣት ሊግ አባል ነው የማደርግህ›› ስለው በድንጋጤ ጥሎ ጠፋ፡፡
አመሰግናሉ፤ ስለ ቃለ መጠይቁ
አደራ ይኼ ቃለ መጠይቅ ከታተመ የሆነ ቦታ አንድ ቅጅ እንዲቀመጥ፡፡ ምናልባት ከሃያ ዓመት በኋላ እንዳገኘው
(መነሻ ሃሳብ Jokes of the Velvet Revolution)
ኳታር፣ ዶሃ
© ይህ ጽሑፍ በአዲስ ጉዳይ መጽሔት የወጣ ነው