አምሳሉ፤ እንኳን ትሞት ትታመምም አይመስለኝ ነበር

 
ጌታቸው ኃይሌ
ኮሌጅቪል፤ ታኅሣሥ 12 ቀን፤ 2006 (12/21/2013)
ፕሮፌሰር አምሳሉ አክሊሉና እኔ አብሮአደግ አብሮጎልመስ፥አብሮአረግ ነን። 1947 . . የእንግሊዝ ፊደል አብረን ከቆጠርንበት ጊዜ አንሥቶ በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርስቲ አንድ ዓይነት ትምህርት ለማስተማር እስከተቀጠርንበት ጊዜ ድረስ በቦታ እንኳን ሳንለያይ አብረን ነበርን። በዚህ አምላክ በመረቀልን ረጅም ጊዜ አንድ ቀንም አንዳችን ሌላውን ቅር የሚያሰኝ ቃል ከአፋችን መውጣቱ ትዝ አይለኝም። የተለያየ ጠባይ ያላቸው ሰዎች መፋቀር፥ መተሳሰብ፥ መረዳዳት፥ እንደሚችሉ የአምሳሉና የእኔ ወዳጅነት ምሳሌ ሊሆን ይችላል። ለጻፍኩት የሕይወት ታሪኬ ርእሱን የአምሳሉና የጌታቸው ታርክ ብለው የተገባ መሆኑን ያነበበው ሁሉ ሊገምት ይችላል። ረጅሙን በወንድማማችነት አብሮ የመኖር ሕይወታችንን ለማስቀረት ደርግና ሞት ሸመቁበት።

አምሳሉን በዚህ ረጅም ዘመን እንደማውቀው፥ ሞት ቀርቶ ሕመም ይደፍረዋል ብየ አልገመትኩም፤ እሱም አይገምትም ነበር። ሙሉ ጤነኛ ነበር፤ እኔ ሐኪም ቤት ስመላለስ፥ እሱ ሐኪም ቤቱን የሚያውቀው እንደኔ ያሉ ሕመምተኞችን ለመጠየቅ ሲሄድ ነበር።አምሳሉ ጤነኛ ብቻ ሳይሆን ሕይወቱ በተግባር የተመላ ነበር። ሥራ ሲወጥን፥ ሥራ  ሲያጣድፍ፥ ሥራሲፈጽም፥ እንቅልፍ አልነበረውም። ሲጫወት፥ ሲያጫውት ሁሉን ያስደስት ነበረ። በዚህ ሁሉ ምክንያት መቶ ዓመት ሳይሞላው ሊሞት ቀርቶሆዴን ጎረበጠኝየሚል እንኳን አይመስለኝም ነበር። ግን በኢሳይያስ አፍ፥እስመ፡ ኢኮነ፡ ምክርየ፡ ከመ፡ ምክርክሙ፤ ወኢኮነ፡ ፍኖትየ፡ ከመ፡ ፍኖትክሙ።” (ሐሳቤ እንደ ሐሳባችሁ አይደለም፤ መንገዴም እንደመንገዳችሁ አይደለም።) የሚለው አምላክ ወንድሜን አምሳሉን፥ እሱ ባሰበው፥ እኛ ባላሰብንበት ዕለት ወሰደው። ሳንሰነባበት ተለያየን። ጽሎቴ ዕለተ ዕረፍቱን የመረጠለት አምላክ ለነፍሱ ከወዳጆቹ ማህል የተደላደለ ቦታ እንዲመርጥላት ነው።
አምሳሉ ሥራ የሚፈጸምለት ታታሪ ሠራተኛ በመሆኑ ብቻ ሳይሆን ብልህና አስተዋይ በመሆኑ ጭምር ነው። በብልህነቱ፥ በዐዋቂነቱ እቀናበት እንደነበረ ከእሱ በቀር ማንም አያውቅም። ሊሠሩ የሚገባቸውን ሥራዎች ማንም ሳያያቸው እሱ ቀድሞ ያያቸዋል። አምሳሉ በዘመኑ ሥልጣኔ በተራመዱት አገሮች በአንዱ ተወልዶ ቢሆን ኖሮ፥ በሀብትም ሆነ በሙያ በዓለም ላይ አሉ ከሚባሉ ታዋቂዎች አንዱ ይሆን ነበር። ሲዘፍን፥ ቲያትር ሲሠራ፥ ያፈዝ ነበረ።
አምሳሉ ቀለመወርቅን በማግኘቱ ዕድለኛ የኖነውን ያህል እሷም አምሳሉን የመሰለ አጫዋችና አፍቃሪ የሕይወት ጓደኛ በማግኘቷ ዕድለኛ ነች። በአካል ቢለያዩም ትዝታውንና ጨዋታውን እያስታወሰች እንዳዲስ ስትስቅ እንደምትኖር እርግጠኛ ነኝ።  
አምሳሉ ቀለመወርቅን ለማግኘት ወዲያ ወዲህ ሲል እኔም ትንሽ ሚና ተጫውቻለሁ፤ ከመልካም ቤተሰብ የተወለደችና ጎልማሳ የምታፈዝ ቆንጆ ልጃገረድ ስለነበረች ለትዳር የሚመኟትና የሚፈልጓት ጥቂቶች አልነበሩም። አንዱ በተለየ ጓደኞቹን አስሰልፎ  ሊያስፈራራሲመጣ አጭር ብትፈልግ አጭር፥ ረጅም ብትፈልግ ረጅም ሆነን መጥተንብሃልና የምትፈልገውን አሳየንና እናሳይ አልነው። ማን እንዳሸነፈ የአምሳሉና የቀለመወርው ልጆች ምስክር ናቸው።
እኔም እንደቀለመወርቅ በጨዋታው ሳስታውሰው እኖራለሁ። በትምህርት ገበታ ላይ ብቻ ሳይሆን አገር ለመጎብኘትም አብረን ብዙ ነገር አይተናል። ኪሳችን የተማሪ ኪስ ስለነበረ፥ አገር የምናየው መንገድ ላይ እየቆምን ባለመኪና ሲመጣ እየለመንን ነበር። የለማኝ መራጭ ስለሌለው፥ የቆመልን ሁሉ ይወስደናል። አንዳንድ ጊዜ ባለመኪናዎቹ ሁለት ሰው ስለማይወስዱ አውላላ ሜዳ ላይ እንለያያለን። ቀጠሯችን ባቡር ጣቢያ ነው። አንድ ቀን ባቡር ጣቢያ ስንገናኝ፥አምሳሉ፤ የዛሬው ጉዞህ እንዴት ነበር?” አልኩት።
እረ እባክህ ተወኝአለ።ምነው?” ብለው፥አንዲት ሴትዮ በዶቅዶቂት አሳፈረችኝአለኝ።ታዲያ ምኑ ነው፥ እረ እባክህ ተወኝ የሚያሰኘው?” ብለው።እንዳልወድቅ ትከሻዋን ነበር የያዝኩት፤ እንደሱ አይደለም፤ ወገቤን ያዝአለችኝ። ልንሄድበት ስንደርስ ልቀቀኝ ባትለኝ እዚያው ተጣብቄ ልቀር ነበርአለኝ።
አይ አምሳሉ፤ ለካ አንተም እንደሌላው ነህ!! ግን የምንጽናናባቸው ብዙ ምክንያቶች አሉን። በጤና ኖረሃል። መልካም ባለቤት፥ መልካም አባት፥ ታማኝ ወዳጅ ሆነሃል። የልጅ ልጅ ስመሃል። በዕውቀትህ የአገርህን ልጆች አገልግለሃል። ለስምህ ሐውልት ተክለሃል። የፈለከውን ለማድረግ አምላክ ዕድል ሰጥቶሃል። ክብሩ ይስፋ። ለዘላለሙ ሕይወት በሚኬድበት መንገድ የሄድከው የማይቀር ቢሆን ነው። ቤተሰብህን፥ ዘመዶችህን፥ ወዳጆችህን እግዚአብሔር ያጽናቸው። እንደኔ ምስጢረኛ አያሳጣቸው።
ምንጊዜም የማይረሳህ ወንድምህ
ጌታቸው ኃይሌ