ሲኖዶሱ ስለ አዲስ ኤጲስ ቆጶሳት ሹመት እንደሚመክር ተጠቆመ

(አዲስ አድማስ፤ ቅጽ 13 ቁጥር 716፤ ጥቅምት ፪ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም.)

Ethiopian_Orhodox church bilden addis_Abeba_2የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ፣ በጥቅምት ወር አጋማሽ በሚያካሂደው የመጀመሪያ መደበኛ ስብሰባው፣ ስለ አዲስ ኤጲስ ቆጶሳት ሹመት ጉዳይ በመምከር የምርጫ ኮሚቴ ሊሠይም እንደሚችል ተጠቆመ፡፡

የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ምንጮች ለአዲስ አድማስ እንደጠቆሙት፣ በቤተ ክርስቲያኒቱ ቀኖና መሠረት የኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ የሚፈጸመው በሕገ ቤተ ክርስቲያን ስለ ኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ በሰፈረው ድንጋጌ መሠረት የመሾሙ አስፈላጊነት በቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ሲታመንበትና ሲወሰን ነው፡፡

ጥቂት የማይባሉ ሊቃነ ጳጳሳት በሞተ ዕረፍት መለየታቸው፣ በዕርግናና በሕመም ሳቢያ የአህጉረ ስብከታቸውን አስተዳደር በብቃትና በቅርበት ለመምራት የማይችሉ ሊቃነ ጳጳሳት መብዛታቸው፣ በውጭና በሀገር ውስጥ የተዋቀሩ የቤተ ክርስቲያኒቱ አህጉረ ስብከት ቁጥር መጨመርና ብዙዎቹም በአንድ ሊቀ ጳጳስ እየተጠቃለሉ መመራታቸው ሐዋርያዊ ተልእኮን ለማፋጠንና ሁለንተናዊ አገልግሎትን ለማስፋት መሰናክል መፍጠሩ ለአዲስ ኤጲስ ቆጶሳት ምርጫና ሹመት በምክንያትነት ተጠቅሷል፡፡

ጥንታዊቷ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በመሠረተ እምነት ከምትተባበራትና ለ1600 ዓመታት እንደ አንድ ሀገረ ስብከት ትቆጠር ከነበረችበት ከግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ማርቆስ ‹ሞግዚትነት› ተለይታ የራሷን መንበረ ፕትርክና (መንበረ ተክለ ሃይማኖት) ከተቀዳጀችበት ከ1951 ዓ.ም ወዲህ ለመጨረሻ ጊዜ የኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ ያካሄደችው በሐምሌ ወር 1997 ዓ.ም. እንደነበር ምንጮቹ አስታውሰዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት በሀገር ውስጥ 53 በውጭ ደግሞ 11 ያህል አህጉረ ስብከት በማዋቀር መንፈሳዊ አገልግሎቷን የምትፈጸመው ቤተ ክርስቲያኒቱ የአህጉረ ስብከቱን አስተዳደር በበላይነት የሚመሩ ከ43 ያላነሱ ሊቃነ ጳጳሳት እንዳሏት ተዘግቧል፡፡ ከእኒህም የሚበዙት አምስተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በኻያ ዓመት ዘመነ ፕትርክናቸው በአንብሮተ እድ የተሾሙ 49 ኤጲስ ቆጶሳት መኾናቸው ታውቋል፡፡

በዜናው ምንጮች እንደተጠቆመው÷ ጥቅምት 12 የሚጀመረው የሲኖዶሱ ምልአተ ጉባኤ መደበኛ ስብሰባ የኤጲስ ቆጶሳቱን ምርጫና ሹመት በአጀንዳነት ይዞ ለመወያየት ከተስማማ የምርጫ ኮሚቴ እንደሚሠይም፣ የተሿሚ ቆሞሳትን ዝርዝር እንደሚያጸድቅና የበዓለ ሢመቱንም ቀን እንደሚወስን ይጠበቃል፡፡ ይህም በስድስተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ዘመነ ፕትርክና የሚፈጸም ቀዳሚው የኤጲስ ቆጶሳት ሹመት ይኾናል ተብሏል፡፡

ከአወዛጋቢው የሲኖዶሱ መከፋፈል አኳያ በቅርብ የሚጠበቀው የአዲስ ኤጲስ ቆጶሳት ሹመት ለቤተ ክርስቲያኒቱ አስተዳደራዊ አንድነት ጥያቄ እንደሚያስነሣ ቢያሰጋም፣ ‹‹በዕቅድ በተያዘው የመዋቅራዊ አደረጃጀትና አሠራር ለውጥ መሠረት የቤተ ክርስቲያኒቱን ሐዋርያዊ ተልእኮ ለማፋጠንና አስተዳደሯን ለማሻሻል ሹመቱ ያለው አስፈላጊነት በመሠረቱ የሚታመንበት ነው፤›› ተብሏል፡፡

ይኹንና ለኤጲስ ቆጶስነት በዕጩነት የሚቀርቡት ቆሞሳት ከነውርና ነቀፋ ነጻ ለመኾናቸው በጥብቅ የሚፈተሽበት፣ የሚለዩበት ሂደት በስፋት ከሚወራው ጥቅመኝነትና ጣልቃ ገብነቶች ተጠብቆ በሕገ ቤተ ክርስቲያን ስለ ኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ በዝርዝር የተደነገገው መመዘኛ በተሟላ ኹኔታ የሚፈጸምበትና የሲኖዶሱ አባላት ብቻ ሳይሆን የምእመናንም ይኹንታ የተካተተበት እንዲኾን ስለ ጉዳዩ አስተያየታቸው የሚሰጡ ወገኖች ያሳስባሉ፡፡

በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ መመዘኛ መሠረት ለኤጲስ ቆጶስነት ብቁ የሚኾኑ መነኮሳት÷ በሥርዐተ ምንኩስና በድንግልና መንኩሰው ለሦስት ዓመታት በመነኮሱበት ገዳም ያገለገሉ፣ ዕድሜያቸው ከ45 – 60 ዓመት የኾናቸው፣ በሃይማኖታቸው ጽኑና በግብረ ገብነታቸው የተመሰገኑ፣ በነገረ መለኮት በቂ ችሎታ ያላቸውና ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን ጠንቅቀው ያወቁ፣ ከሙሉ አካልና ጤንነት ጋራ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት በመፈጸም የአስተዳደር ልምድ ያላቸው መኾን ይገባቸዋል፡፡