የአእምሮዎን ጤና ለመጠበቅ 10 ነጥቦች – ወንድሙ ነጋሽ
የአእምሮዎን ጤና ለመጠበቅ 10 ነጥቦች – ወንድሙ ነጋሽ ( “የአእምሮ ጉዳይ” የተሰኘው መጽሐፍ ደራሲ )
የአእምሮዎን ጤና ለመጠበቅ 10 ነጥቦች
1. አእምሮ ማዘዣ ጣቢያ ነው፡፡ በቫይረስ መጠቃት የለበትም፡፡ ሁልጊዜ ሊጸዳ ይገባዋል፡፡ አእምሮ ከተወዛገበ ሌሎች የሰውነት አካላት መግባባት ያቅታቸዋል፡፡ አእምሮዎ በአስቀያሚ ቫይረሶች እንዳይጠቃ ማታ ማታ “ስካን” ያድርጉት፡፡ እንዴት ካሉ- በቀን ዉስጥ ለ30 ደቂቃ ለብቻዎ ሆነው ወደዉስጥ ያሰላስሉ፡፡ በቀን ዉስጥ ጥሞና (meditation) ለ30 ደቂቃ ያስፈልጎዋታል፡፡ ደስ የሚሉዎትን ነገር እያሰቡ አእምሮዎን ዘና ያድርጉት፡፡
2. አእምሮ ዕለታዊ ተግባራትን እንዳያከናውን ከሚፈትኑት ነገሮች አንዱ መጠጥ ነው፡፡ ሌላው ደግሞ አደገኛ ዕጽ ነው፡፡ ሌላው ደግሞ ጫት ነው፡፡ እነዚህ በሙሉ ይነስም ይብዛ አእምሮን ይመርዛሉ፡፡ ማናቸውም አእምሮን ጤናማ ባልሆነ መልኩ የሚያነቃቁ ዕጾች ተግባሩን ያውኩታል፡፡ ያስወግዷቸው፡፡
3. አእምሮ በቀን ዉስጥ ምን መስራት እንዳለበት ካልተነገረው ድብርት ዉስጥ ይገባል፡፡ በቀን ዉስጥ ምን መከወን እንዳለብዎ፣ ምን ምን ማሳካት እንደሚፈልጉ ይንገሩት፡፡ ያንን እንዳሳካ ሲገባው አእምሮ ዘና ይላል፡፡
4. አእምሮዎ ልክ እንደ ጡንቻ ነው፡፡ ብዙ ሥራ ባሰሩት ቁጥር እየጠነከረ ይመጣል፡፡ አዳዲስ ነገሮችን መማር ይፈልጋል፣ አዳዲስ ተግዳሮቶች፣ አዳዲስ ፈተናዎች፣ አዳዲስ ጥበቦች እንዲማር እድል ይስጡት፡፡ በዚህ ዘመን 5+9 =14 የሚል ሂሳብ ለመስራት እንኳን ካልኩሌተር ነው የምንጠቀመው፡፡ የቅርብ ጓደኛችንን ስልክ በቃላችን ለመያዝ እንሰንፋለን፡፡ አእምሮ ከሰነፈ ይለግማል፡፡ አእምሯችሁን ቦዘኔ አታድርጉት፡፡ እንዳይዝግባችሁ መጽሐፍ አንብቡለት፡፡
5. አእምሮ ጥሩ ምግቦች ስል እንዲሆን ያደርጉታል፡፡ የአሳ ዘይትና ሌሎች የተመጣጠኑ ምግቦችን በቀን በቀን ካገኘ ሥራ ማቀላጠፍ ያውቅበታል፡፡ በቂ ዉኃ መጠጣት ለአእምሮ እንደ ግሪስ ያገለግላል፡፡
6. አእምሮ በቫይረስ ይጠቃል፡፡ የአእምሮ ቫይረስ ምን እንደሆነ ያውቃሉ? አሉታዊ አስተሳሰቦች፡፡ ምቀኝነት፣ ክፋት ማሰብ፣ በማይረቡ ነገሮች መጨነቅ አእምሮን ያዉካሉ፡፡ ይህን ቫይረስ ለማጽዳት መልካም መልካሙን ማሰብ ብቻ ይበቃል፡፡
7. ቁርስ በፍጹም አይዝለሉ፡፡ መኪናዎ ማለዳ ተነስተው እንደሚያሞቋት ሁሉ አእምሮዎንም በአሪፍ ቁርስ ያነቃቁት፡፡ ቀኑን ሙሉ በንቃት እንዲሰራ ጥሩ ቁርስ ያስፈልገዋል፡፡
8. ተሸፋፍነው አይተኙ፡፡ አእምሮ እጅግ ብዙ መጠን ያለው ኦክሲጂን የሚፈልግ የሰውነት ክፍል ነው፡፡ ሲታፈን ግራ ይገባዋል፡፡ መኪና የሚበዛባቸው ስፍራዎች፣ ኢንደስተሪዎች፣ ብዙ ሲጋራ የሚጨስባቸው አካባቢዎችን ያስወግዱ፡፡ በተቃራኒው መናፈሻ፣ አረንጓዴ ተክሎች የሚበዙባቸው ሜዳማ ስፍራዎች የእግር ጉዞ ቢያደርጉ አእምሮ በጣም ያመሰግንዎታል፡፡
9. የከሰል ጭስ ለአእምሮ መርዝ ነው፡፡ ብዙ ሰዎች ይህን ባለመረዳት ቤታቸውን በእጣንና በከሰል ጭስ ያፍናሉ፡፡ በነገታው ኃይለኛ ራስ ምታት ያማቸዋል፡፡ የከሰል ጭስ አእምሮን ሊገድለው ይችላልና ይጠንቀቁ፡፡
10. ለእርስዎ የማያስደስትዎትን ነገር ለሰው ሲሉ ብቻ አያድርጉ፡፡ የማያምኑበትን ነገር በፍጹም አይተግብሩ፡፡ ወደፊት ለጸጸት የሚዳርግዎትን መልካም ያልሆነ ተግባር በድብቅም ቢሆን አይስሩ፡፡ ፀፀትና የሕሊና ወቀሳ ለአእምሮ መርዛማ ነገሮች ናቸው፡፡ ሙሰና፣ ከትዳርዎ ዉጭ ማማገጥ፣ በሰው ላይ ተንኮልና ሴራ መፈፀም አእምሮን እስር ቤት ዉስጥ ማጎር ማለት ነው፡፡ አእምሮ ሰላሙን አጥቶ ሰላምዎን እንዳይነሳዎ መልካም መልካሙን ብቻ ያድርጉ፡፡
®አቶ ወንድሙ ነጋሽ ነዋሪነታቸው በእንግሊዝ ሲሆን “የአእምሮ ጉዳይ” የተሰኘው መጽሐፍ ደራሲ ናቸው፡፡ በአእምሮ ጤና ዙርያ በራስ ተነሳሽነት ጥናትና ምርምር እንዲሁም ተያያዥ የበጎ አድራጎት ሥራዎችን ይሰራሉ፡፡
