ሰላማዊ ሰልፉን ተከትሎ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሰማያዊ ፓርቲ ከፍተኛ አመራርን ከስራ አገደ

Image
የሰማያዊ ፓርቲ የወጣቶች ጉዳይ ኃላፊ አቶ እያስፔድ ተስፋዬ ከሚሰራበት የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የአዳር ሰላማዊ ሰልፉን ተከትሎ በደረሰበት እስር ምክንያት ከስራው ታገደ፡፡ እያስፔድ ተስፋዬ በሶስተኛ ፖሊስ ጣቢያ ጨለማና ቀዝቃዛ ክፍል ታስረው ከነበሩት አመራሮች መካከል አንዱ ሲሆን ከእስር ከተፈታ በኋላ ታስሮ ስለመቆየቱ ማስረጃ ቢወስድም ለ15 ቀን ከስራ ታግዶ እንዲቆይ ተደርጓል፡፡

‹‹ታስሬ መቆየቴን የሚያሳይ ማስረጃ ወደምሰራበት ቅርንጫፍ ስወስድ ከእኛ አቅም በላይ ስለሆነ ወደ ዲስትሪክት ውሰድ ተባልኩ፡፡ ዲስትሪክት ስወስድ የንግድ ባንክ ዳይሬክተር የሰው ኃይል አስተዳደር ማመልከቻና ታስረህ የቆየህበትን ማስረጃ አስገባና እነሱ ወደ ስራ ገበታህ ተመለስ ካሉህ ነው የምትመለስ፤ እነሱ ተመለስ እስኪሉህ ድረስ ግን ወደ ስራ ገበታ መመለስ አትችልም አሉኝ፡፡ ባሉኝ መሰረትም ለሰው ኃይል አስተዳደር ደብዳቤና ከፖሊስ ጣቢያ የተሰጠህን ማስረጃ ወሰድኩ፡፡ እሱ እስኪያየው ድረስ ተብሎ አንድ ቀን ቀጠሮ ተሰጠኝ›› የሚለው እያስፔድ በቀጠሮው መሰረት ሲሄድ ጉዳዩ ለቅሬታ ሰሚ ኮሜቴ እንደተላከ፣ ቅሬታ ሰሚ ኮሚቴ አባሎች ስልጣና ላይ በመሆናቸው ለ15 ቀን ስራ መግባት እንደማይችልና ለታገደበት ቀናትም ደመወዝም እንደማይከፈል እንደተገለጸለት ለነገረ ኢትዮጵያ አስረድቷል፡፡

ቀደም ሲል የሰላማዊ ሰልፉን ተከትሎ አቶ ወሮታው ዋሴ ከኢትዮጵያ አየር መንገድ የተባረሩ መሆናቸው ይታወሳል፡፡